ከነቢይነታቸው ማረጋገጫዎች ጥቂቱ

ከነቢይነታቸው  ማረጋገጫዎች ጥቂቱ

1- አንድ አላህን (ሱ.ወ.) ብቻ ለማምለክና ከርሱ

በስተቀር ሌላ እንዳይመለክ ጥሪ ማድረጋቸው፣በዚህም ከሁሉም ነቢያት ጋር አንድ መሆናቸው አንዱ የነቢይነታቸው ማረጋገጫ ነው። ሙሳ ዒሳና ሙሐመድ  ያስተማሩትን ትክክለኛ እምነት፣ሕግጋትና ጠቃሚ ትምርቶችን አነጻጽሮ የተመለከተ ሰው፣ሁሉም ከአንድ ምንጭ ማለትም ከነቢያዊ ምንጭ የተቀዱ መሆናቸውን ይረዳል።

2- ለአላህ ነቢያት ብቻ እንጂ የማይከሰቱ ተአምራትና ግልጽ ምልክቶች ያሳዩ መሆናቸው ሌላው ማረጋገጫ ነው።

ለሕዝቦቻቸው አስረጅ ታምርና ለእውነተኛነታቸው ማረጋገጫ ይሆን ዘንድ ከተለምዶ ውጭ የሆነ ትንግርታዊ ነገር በቀደሙት ነቢያት እጅ እንዲከሰት ማድረግ የአላህ (ሱ.ወ.) ሕግ ነበር። የያንዳንዱ ነቢይ ታምርም የተላከበት ሕዝብ ከተራቀቀበት ነገር ዓይነት ይሆን ነበር። የነቢዩ ሙሳ  ታምር የተላኩበት ሕዝብ የተራቀቀበት ነገር ማለትም ድግምት ነበር። የነቢዩ ዒሳ  ሕዝብ ደግሞ በሕክምናና በመድሃኒት ጉዳዮች የገነነ ስለነበር ለነቢዩ  የተሰጣቸው ታምር አስቸጋሪ የሆኑ በሽታዎችን መፈወስና በአላህ (ሱ.ወ.) ፈቃድም ሙታንን እስከማስነሳት የደረሰ ነበር። እነዚህ በሙሉ ቁሳዊ ታምራት ከመሆናቸውም ባሻገር በጊዜና በቦታ የተገደቡ ነበር። የዓለም አቀፋዊነትና የቀጣይነት ባሕርይ የላቸውም።

ከነቢዩ ሙሐመድ  ታምሮች መካከልም መሰል ቁሳዊ ታምሮች ሲገኙ፣ከጣቶቻቸው መካከል ውሃ መፍለቁ፣ጥቂቱ ምግብ አብሯቸው የነበሩ ሙስሊሞች እንዲያጠግብ በእጃቸው ላይ መብዛቱና ተርፎም መቅረቱ፣ሰራዊቱ በሙሉ እስኪጠጣና ውዱእ እስኪያደርግ ጥቂቱ ውሃ በዝቶ መበራከቱ፣ለጁሙዓ ኹጥባ ይደገፉበት የነበረው የተምር ግንድ የዲስኩር ማድረጊያ ምንበር ተሰርቶላቸው ሲለዩት ግንዱ እዬዬ ማለቱ፣መካ ውስጥ ድንጋይ ሰላምታ ያቀረበላቸው መሆኑ፣ዛፍ ወደሳቸው መምራቱ፣የአሸዋ በመዳፎቻቸው ውስጥ አላህን ማወደስ፣በአላህ ፈቃድ ሕሙማንን መፈወሳቸውና ሌሎችም ይገኛሉ።

ከነዚያ ቁሳዊ ታምራት መካከል የሌሊት ጉዞና የዕርገትን (የእስራእና የምዕራጅ) ተአምርን ቅዱስ ቁርኣን መዝግቦታል። ተአምሩ በአንድ ሌሊት ከመካው የተከበረ መስጊድ እየሩሳሌም ወደሚገኘው የአልአቅሷ መስጊድ እንዲሄዱና ከዚያ ሰባቱን ሰማያት እስኪያልፉ ድረስ ወደ ሰማየ ሰማያት ማረጋቸውን የሚመለከት ሲሆን አላህ (ሱ.ወ.) እንዲህ ብሏል፦

{ያ ባሪያውን (ሙሐመድን) ከተከበረው መስጊድ፣ወደዚያ ዙሪያውን ወደ ባረክነው ወደ ሩቁ መስጊድ በሌሊት ውስጥ ያስኼደው (ጌታ) ጥራት ይገባው፤ከታምራቶቻችን ልናሳየው፣(አስኼድነው)፤እነሆ እርሱ (አላህ) ሰሚው፣ተመልካቹ ነው።}[አል እስራእ፡1]

የጨረቃ ለሁለት መገመስም በቁርኣን የተዘገበ ሌላው ተአምራቸው ነው። አላህ (ሱ.ወ.) እንዲህ ብሏል፦

{ሰዓቲቱ (የትንሣኤ ቀን) ተቃረበች፤ጨረቃም ተገመሰ፤}[አል ቀመር፡1]

ጣዖታውያን ሙሽሪኮች ስለ እውነተኛነታቸው ማረጋገጫ የሚሆን ግልጽ ተአምር እንዲያሳዩዋቸው ነቢዩን  ጠይቀው በዚህ ረገድ በተለይ ጨረቃን ለሁለት እንድትገመስና ይህን ካደረጉ ለማመን ቃል ገቡላቸው። ዕለቱ ጨረቃ ሙሉ የምትሆንበት የወሩ አስራ አራተኛ ሌሊት ነበር። የአላህ መልክተኛ  ሰዎቹ የጠየቁትን ታምር ይሰጣቸው ዘንድ አላህን ለመኑትና ጨረቃ ለሁለት ተገመሰች፤ግማሹ በሶፋ ተራራ ግማሹ ደግሞ በትይዩው በሚገኘው የቀይቀዓን ተራራ በላይ ሆና ታየ። ይህ ታላቅ ታምር ከተከሰተ በኋላ ግን የቁረይሽ ሙሽሪኮች ድግምት አድርገው ወሰዱት እንጅ አላመኑበትም። ስልጣናቸው ከሐቅ ፊት መቆም ተስኖት ሲናድ በአላህ ሃይማኖት ያስተባበሉ ሰዎች የሚያደርጉት የተለመደ ተግባር ነው። በዚህ ጊዜ መርሆችን በማጣመም ወይም እውነታን በመደበቅ በሃይማኖቱ ላይ ተንኮል ከመሸረብና ደንቃራ ሆነው ከፊቱ ከመቆም አይመለሱም። ይህን የሚያደርጉትም ሃይማኖቱን ለማጥፋት በቂ መስሎ ስለሚታያቸው ነው። አላህ (ሱ.ወ.) እንዲህ ብሏል፦

{ታምርንንም ቢያዩ (ከእምነት) ይዞራሉ፤(ይህ) ዘውታሪ ድግምት ነውም ይላሉ። አስተባበሉም፤ዝንባሌዎቻቸውንም ተከተሉ፤ነገርም ሁሉ (ወሰን አለው)፤ረጊ ነው።}[አል ቀመር፡2-3]

3- ቁርኣን፦

ከታምራቶቹ ሁሉ ታላቁ፣ዘመናትን ተሸጋሪና ቀጣይነት ያለው ዘላለማዊ፣ከነቢይነት ማረጋገጫ ምልክቶች አንዱና በጊዜና በስፍራ ያልተገደበ ሕሊናዊ ተአምር ነው። ይህም በማያነብና በማይጽፍ ሰው ላይ አላህ (ሱ.ወ.) ያወረደው፣መሰሉን መጽሐፍ ወይም ከምዕራፎቹ አንዱን ምዕራፍ እንኳ እንዲያመጡ ለዐረብ የቋንቋ ሊቆች የአታደርጉትም ፈታኝ ጥያቄ ቀርቦ ማንም ያልመለሰው ተአምራዊና አሸናፊ ሕያው መጽሐፍ በመሆኑ ነው። የቁርኣንን አቻ ሊገኝለት ያልቻለ ኃያል አሸናፊነትና ታምርነት በሐቅ ላይ ያመጸ ትእቢተኛ እንጅ ማንም ሊክድ አይችልም። በቋንቋ ምጥቀቱ፣በስነጽሑፋዊ ውበቱ፣በአደረጃጀቱና በስልቱ፣እውስጡ ባካተታቸው ያለፉና ወደፊት የሚመጡ ጉዳዮች፣በያዛቸው የጸኑ ሕግጋት፣በተራቀቁ ስነምግባራት፣በቅን መመሪያው፣በብርሃኑና በበረከቱ . . ተአምራዊ ሕያው መጽሐፍ ነው።

ዛሬ እየተደረሰባቸው ያሉትና ቀደም ሲል የሚታወቁ ያልነበሩ ሳይንሳዊ ግኝቶች ቁርኣን ውስጥ ከሰፈሩት እውነታዎች ጋር ሙሉ በሙሉ የሚጣጣሙ ሆነው መገኘታቸውም የነቢዩ ሙሐመድን  ነቢይነት የሚያረጋግጡ ግልጽ ማስረጃዎች ናቸው። በዚህ ረገድ ዘመናዊ ሳይንስ ጽንስ በማሕጸን ውስጥ የሚያልፍባቸውን የእድገት ደረጃዎች አስመልክቶ የደረሰበት ግኝት፣በባሕር ጨዋማ ውሃና በመደበኛው ውሃ መካከል መደበላለቅ እንዳይኖር መለያ መኖሩን የሚመለከተውና ሌሎችም ሳይንሳዊ ቁርኣናዊ እውነታዎች ይገኛሉ። ከሁሉም በላይ ቁርኣን ከአላህ (ሱ.ወ.) ዘንድ የተላለፈ ስለመሆኑ ታላቁ ማስረጃ ለአስራ አራት ምእተ ዓመታት ከመዛባት ከመለዋወጥ፣ከመከለስና ከመበረዝ ተጠብቆ መኖሩና አንባቢው ያሻውን ያህል ቢደጋግመው ፈጽሞ የማይሰለች መሆኑ ነው። አላህ (ሱ.ወ.) እንዲህ ብሏል፦

{እኛ ቁርኣንን እኛው አወረድነው፤እኛም ለርሱ ጠባቂዎቹ ነን።}[አል ሕጅር፡9]

ቁርኣንን በመጠበቁም ትክክለኛውን ዐቂዳ (እምነት) ጠብቋል። የተሟላ ሕግጋቱንም አካቶበታል። በቁርኣን መሠረት ላይም ምርጥ ኡምማ (ሕዝብ) አንጾአል። በዚህም የነቢዩ ሙሐመድ  ተአምር ከተቀሩት ነቢያት ወንድሞቻቸው ተአምራት በኃያልነቱ፣በዓለም አቀፋዊነቱና በዘላላማዊነቱ የተለየ ይሆናል። የአታደርጉትም ፈታኝ ጥያቄም ለሁሌም እንደቀረበ ይቀጥላል፣የቁርኣንን መሰል ማምጣት ያለ መቻል ሽንፈትም እንደዚሁ እስከ ትንሣኤ ቀን ድረስ ቀጣይ ይሆናል። አላህ (ሱ.ወ.) እንዲህ ብሏል፦

{፦ ሰዎችም ጋኔኖችም የዚህን ቁርኣን ብጤ በማምጣት ላይ ቢሰባሰቡ፣ከፊላቸው ለከፊሉ ረዳት ቢኾንም እንኳ ብጤውን አያመጡም፤በላቸው።}[አል እስራእ፡88]

4- ነቢዩ  ወደፊት ስለሚከሰቱት የዓለምና የሀገራት አያሌ ጉዳዮች የተነበዩ ሲሆን እርሳቸው እንደተናገሩት ሆነው በትክክል ተከስተዋል።

ከነዚህ መካከል ሻም፣ዒራቅና ቆስጠንጢኒያ (ቱርክ) ድል ሆነው የሚያዙ መሆናቸው አንዱ ነበር። ከኣደም  ጀምሮ እሰከ ኑሕ፣ኢብራሂም፣ሙሳና ዒሳ  ዘመን ስለነበሩ የቀደሙ ሕዝቦችና ነቢዮቻቸው ከመልክተኞቻቸው ጋር ስለነበሩባቸው ሁኔታዎችም ተናግረዋል። ወደፊት ስለሚከሰቱት ነገሮች ተናግረውም በተነበዩት መሰረት ተፈጽመዋል። ከነዚህ መካከል ፔርሽያ በሮማውያን ላይ ድል በተቀዳጀች ጊዜ አላህ (ሱ.ወ.) ሮማውያን ከጥቂት ዓመታት በኋላ ፔርሽያውያን ድል እንዲሚያደርጉ ማሳወቁ አንዱ ነው። አላህ (ሱ.ወ.) ይህን በማስመልከት እንዲህ ብሏል፦

{አ.ለ.መ. (አሊፍ ላም ሚም)። ሩም ተሸነፈች። በጣም ቅርብ በኾነችው ምድር። እነሱም ከመሸነፋቸው በኋላ በእርግጥ ያሸንፋሉ። በጥቂት ዓመታት ውስጥ (ያሸንፋሉ)፤ትእዛዙ በፊትም በኋላም የአላህ ነው። በዚያ ቀንም ምእመናን ይደሰታሉ፤በአላህ ርዳታ (ይደሰታሉ)፤የሚሻውን ሰው ይረዳል፤እርሱም አሸናፊው፣አዛኙ ነው። አላህ ርዳታን ቀጠረ [ለመርዳት ቃል ገባ]፤አላህ ቀጠሮውን አያፈርስም፤ግን አብዛኞቹ ሰዎች አያውቁም። ከቅርቢቱ ሕይወት ግልጹን ብቻ ያውቃሉ፤እነርሱም ከኋላኛይቱ ዓለም ዘንጊዎች ናቸው።}[አልሩም፡1-7]

ይህ ትንቢትም በትክክል አላህ (ሱ.ወ.) በተናገረው መሠረት በተግባር ተፈጽሟል።

5- ቀደምት ነቢዮች [በሁሉም ላይ የአላህ ሰላም ይውረድ] የነቢዩ ሙሐመድን  መምጣት ከረዥም ዘመናት በፊት ተንብየዋል።

የሚላኩበትን ሁኔታና አገራቸውን፣ሕዝቦችና ነገሥታት በርሳቸውና በኡመታቸው እንዴት እንደሚረቱ፣ሃይማኖታቸው እንዴት እንደሚስፋፋም ገልጸዋል።

6- የነቢያት መደምደሚያ መሆናቸውና ባይላኩ ኖሮ፣እንደሚመጡ ያበሰሩ ነቢያት ትንቢቶችም ውድቅ ይሆን የነበረ መሆኑ።

7- ነቢዩ  በተላኩበት ዘመን የነበሩና ሕሊናቸው በጭፍን ወገንተኝነት ያልታወረ እንደ መነኩሴው በሂራ፣

ወረቀህ ብን ነውፈል፣ሰልማን አልፋሪሲ፣ዐብዱላህ ብን ሰላምና ዘይድ ብን ሰዕናህ የመሳሰሉ አንዳንድ የመጽሐፉ ባለቤቶች፣የነቢዩ ሙሐመድን  እውነተኛነትና በኦሪትና በወንጌልም ውስጥ የተወሱ መሆናቸውን መስክረዋል።

8- በተዋጓቸው ሕዝቦች ላይ ድል መቀዳጀታቸውም ከነቢይነት ማረጋገጫ ምልክቶች አንዱ ነው።

ለምን ቢባል አንድ ሰው በሐሰት ከአላህ የተላክሁ ነኝ እያለ፣አላህ (ሱ.ወ.) እገዛውን ሊሰጠው፣ጠላቶቹን ድል ሊያደርግለትና ጥሪው ተሰራጭቶ አያሌ ተከታዮችን ማፍራት የማይታሰብ በመሆኑ ነው። ይህ እውን ሊሆን የሚችለው በእውነተኛ ነቢይ አማካይነት ብቻ ነው።

9- ነቢዩ  በአምልኮአቸው፣በቁጥብነታቸው፣በእውነተኛነታቸው፣በምስጉን ግለታሪካቸው፣በምሉእ ሰብእናቸው፣በምጡቅ ስነምግባራቸው፣ . . የነበሩበት አጠቃላይ ሁኔታቸው ሌላው የነቢይነታቸው ማረጋገጫ ነው።

ጌታቸው አላህ (ሱ.ወ.) በመልካምና ውብ ባሕርያት እንዲታነጹ አድርጓቸዋል፦

{አንተም በታላቅ ጠባይ ላይ ነህ።}[አልቀለም፡4]

ይህ ሊሆን የሚችለው ለእውነተኛ የአላህ ነቢይ ብቻ ነው።

10- የሙሐመድ  ነቢይነትና ታምራታቸው ከትውልድ ወደ ትውልድ የተላለፈበት ተከታታይነትና ቀጣይነት ያለው አዘጋገብ፤የነቢያትን ሁኔታና ታሪኮቻቸውን ያጠና ሰው፣የተቀሩት ነቢያት ነቢይነት በተረጋገጠባቸው መንገዶች ሁሉ የሙሐመድ  ነቢይነት በበለጠና በተጠናከረ ሁኔታ መረጋገጡን ይረዳል።

የሙሳና የዒሳ  ነቢይነት ተረጋግጦ የተላለፈበትን ተከታታይነትና ቀጣይነት ያለውን መንገድ ብንመለከት፣የሙሐመድ  ነቢይነት የተላላለፈበት ዘገባ የበለጠ ጥንካሬ፣የበለጠ ተአማኒነትና ከዘመንም አንጻር ይበልጥ ቅርበት ባለው ዘገባ መተላለፉን በቀላሉ መገንዘብ እንችላለን። የተሰጧቸው ታአምራቶችና ማረጋገጫ ምልክቶችም እንደዚሁ ተመሳሳይ መሆን ብቻ ሳይሆን የሙሐመድን  በተመለከተ ይበልጥ ታላቅና ዘላለማዊ ቀጣይነት ያላቸው ናቸው። ከሁሉም ታላቁና ኃያሉ የሙሐመድ  ተአምርም በማያቋርጥ ሁኔታ በጽሑፍና በድምጽ ከትውልድ ወደ ትውልድ መተላለፉን የቀጠለው ታላቁ ቁርኣን ነው።

11- የነቢዩ ሙሐመድ  የማያነቡና የማይጽፉ ነቢይ መሆንም ከተአምራቶቻቸው አመላካቾች አንደኛው ነው። አላህ (ሱ.ወ.) ሙሐመድን  የማያነብና የማይጽፍ

ነቢይ አድርጎ የላካቸው ሲሆን ይህም ቅዱስ ቁርኣን ከአላህ የተላለፈላቸው ስለመሆኑ ብርቱ ማስረጃ ነው። በተለይም ብዙ ዓመታትን በሕዝባቸው መካከል የኖሩ በመሆኑ ነቢዩ ማንበብና መጻፍን የተማሩ ቢሆኑ ኖሮ ሙሽሪኮቹ የገዛ ራሱ ፈጠራ ነው ብለው በሞገቱ ነበር። አላህ (ሱ.ወ.) እንዲህ ብሏል፦

{እንደዚሁም ወዳንተ መጽሐፍን አወረድን፤እነዚያም መጽሐፍን የሰጠናቸው በርሱ ያምናሉ፤ከነዚህም (ከመካ ሰዎች) በርሱ የሚያምኑ አልሉ፤በታምራቶቻችንም ከሓዲዎቹ እንጂ ማንም አይክድም። ከርሱ በፊትም መጽሐፍን የምታነብ፣በቀኝህም የምትጽፈው፣አልነበርክም፤ያን ጊዜ አጥፊዎቹ በእርግጥ በተጠራጠሩ ነበር።}[አልዐንከቡት፡47-48]

ነቢዩ  ይዘው የመጡት መልክት ከአላህ ዘንድ የተላለፈላቸው እንጂ ከራሳቸው አለመሆኑን በማረጋገጥም አላህ (ሱ.ወ.) እንዲህ ብሏል፦

{ {እርሱ ያ በመሃይሞች ውስጥ አንቀጾቹን (ቁርአንን)፣በነርሱ ላይ የሚያነብላቸው፣(ከማጋራት) የሚያጠራቸውም፣መጽሐፍንና ጥበብን የሚያስተምራቸው የኾነን መልክተኛ (ሙሐመድን) ከነሱው ውስጥ የላከ ነው፤እነርሱም ከርሱ በፊት በግልጽ ስሕተት ውስጥ ነበሩ።}[አል ጁሙዓ፡2]

የማያነብና የማይጽፈው መልክተኛ ነቢይ መገለጫ ባህርያትም፣የአላህን አንቀጾች ለማይማን ሕዝቦች የሚያሰማ፣የሚያጠራቸውና ነቢያት ለሕዝቦቻቸው ያደርጉት እንደነበረው ሁሉ መጽሐፉን የሚያሳውቃቸው፣ቀደምት መልክተኞች ለሕዝቦቻቸው ያስተማሩትን ጥበብም የሚያስተምራቸው መሆኑን ቁርኣን ይገልጻል። ይህ ሁሉ የዚህ ነቢይ  የማያነብና የማይጽፍ መሆን በራሱ ታላቅ ተአምር መሆኑን፣ያልተማሩ ሆነው የተማሩ የነበሩ ቀደምት ነቢያት ለሕዝቦቻቸው ይዘው የመጡትን ሁሉ ለሕዝባቸው በተሟላ መልኩ ይዘው መምጣታቸው፣ሙሳን  ከመሳሰሉ የሚያነቡና የሚጽፉ ነቢያት ካሳዩት ታምርም የበለጠና የላቀ ታምር ይሆናል።