ለውጥና ሽግግር

ለውጥና ሽግግር

ለውጥና ሽግግር (1)

ጆርጅ አደምን ለማግኘት ወደ ካፌቴሪያው አመራ፣ግን አላገኘውም። አስተናጋጁን ሲጠይቅ ዛሬ ያልመጣ መሆኑንና ለምን እንደ ቀረ እንደማያውቅ ነገረው . .

 

- ትናንት ተገናኝተን ለዛሬ ቀጠሮ ይዘን ነበር።

- ያወቅነው ነገር የለም። አለመምጣቱ የሚገርም ነው፤ለማንኛውም ግን ነገ ይመጣ ይሆናል።

ጆርጅ ካፌውን ለቆ ሄደ፤በቀጥታ ወደ አደም ቤት በማምራት በሩን አንኳኳ፣የሚመልስ ሰው አልነበረም

። ስልክ ለመደወል ሲሞክር ሞባይሉ ዝግ ነው . . ነገሩ እያሳሰበው ወደ ቤቱ ተመልሶ ሄደ . .

- ካትሪና . . አደም ጠፋ፣በሥራ ቦታውም ሆነ እቤቱም ሄጄ ላገኘው አልቻልኩም፣ሞባይሉም ዝግ ነው።

- ይህ የመጀመሪያው አይደለም፣ትዝ ካለህ ከዚህ ቀደምም እንደዚሁ ጠፍቶብህ አልነበረም?

- ልክ ነሽ፣በሽብር ፍንዳታው ምክንያት በሀሰት ተጠርጥረው ታስረው ከነበሩት መካከል አንዱ ነበር መሰለኝ፣ነገር ግን ሙስሊም መሆኑን አላውቅም ነበር።

- ከአደም ጋር ብዙ አንተዋወቅም፣ግን በጣም ነው የማከብረው። በታመምክ ጊዜ ላንተ የነበረውን አዘኔታና እንድትፈወስ የነበረውን ከፍተኛ ጉጉት አስተውያለሁ። የካኽን ወራዳ ባህሪ ያስተናገደበትን ጨዋ ስነ ምግባሩንም ተመልክቻለሁ።

- አንቺ ስለ እርሱ የማታውቂውና እኔ በሚገባ የማውቀው ለኔ በጎውን የሚመኝልኝና የሚያስብልኝ ፍጹም ወዳጅ መሆኑ ነው። ይህን ከአንድ በላይ በሆኑ አጋጣሚዎች ለማየት ችያለሁ፤ይህን ሁሉ ክብካቤና ፍጹምነት ለምን እንደሚሰጠኝ ሳስብ እገረማለሁ።

- ምኑ ነው የሚገርመው?!

- ክርስቲያን አለመሆኑን እስካወቅበት ጊዜ ድረስ የሚገርም አልነበረም።

- አልገባኝም፣ ለምን? !

- ወደ ቴል አቪቭ እንድሄድና አይሁዳዊነትን እንዳጠና ይገፋፋኝ የነበረው እርሱ ነው። ክርስትናን እንዳጠናና ወደ ሮም እንድሄድ የገፋፋኝም እርሱ ነው። ለራሱ ክርስቲያን ሳይሆን ይህን እንዴት ሊያደርግ ቻለ?

- ምናልባት ይህ በራስ የመተማመን ምልክት ሊሆን ይችላል።

- ወይም በስልቱ እርግጠኝነትና በሚከተለው መንገድ ካለው በራስ የመተማመን መንፈስ የመነጨ ሊሆን ይችላል።

- ሊሆን ይችላል፤በጥቅሉ ግን ቁርኣን በጣም ልዩ የሆነ መጽሐፍ ነው። በመልክትህ እንደ ጠቀስከው በዚህ ሳምንት አታነበውም?

- ቀደም ብዬ እንደ ነገርኩሽ ማንበብ እፈልግ ነበር፣የካኽ ጉዳይ ነው የረበሸኝ፣አሁን ደግሞ የአደም መሰወር። ለማንኛውም ወስጄ እንዳነበው አንብበሽ ጨረስሽ?

- አዎ ጨርሻለሁ፣አንዳንድ ነገሮችን ግን ደግሜ ማየት የግድ ይመስለኛል። ሌላ ቅጂ እንዲገዛልህ ትፈልጋለህ?

- በመጽሐፍት መሸጫ መደብር ካለፍሽ አንድ ግዥልኝ። በነገራችን ላይ ቁርኣን መጀመሪያ የተጻፈው በምን ቋንቋ ነው?

- በዐረብኛ ቋንቋ ብቻ ነው።

- ታድያ እንዴት ነው ያነበብሽው?

- ትርጉሙን ነው የማነበው።

- ብሉይና አዲስ ኪዳንንም ትርጉማቸውን አይደለም አነበብን የምንለው? ልዩነቱ ምኑ ላይ ነው?

- በላክልን ደብዳቤ በጠየቅከን መሰረት ጉዳዩን በዚህ ርእስ ላይ አንብቤ ለመመርመር ችያለሁ። እናም ቁርኣን በታሪክ ውስጥ አቻ በሌለው የተአማኒነት ሁኔታ ለዘመናት ከትውልድ ወደ ትውልድ የተላለፈ መጽሐፍ ነው። ከነብያቸው ከሙሐመድ ቁጥራቸው የበዛ ሰዎች ሰምተውና መዝግበው ለሌሎች አስተላልፉት፣በዚህ ሁኔታ ሲወርድ ሲዋረድ ነው እስከ ዛሬው ዘመናችን የደረሰው። ምንም ዓይነት ስህተትም ሆነ የመለወጥ ችግር ፈጽሞ ሳይደርስበት ባለበት ተጠብቆ ለመኖር የቻለ መጽሐፍ ነው። ትርጉሞቹ ግን ስህተት ሊኖሩባቸው ይችላል ።

- እንዴት?

- አያሌ ቀሳውስት የቁርኣንን ፍች የተረጎሙ ሲሆን ትርጉማቸው ግን በዘፈቀደ የተሰራ ነው። አንዳንዶቹ ትርጉሞችም ስህተት አለባቸው።

- እናም . . ቁርኣን በተለይ ለዐረቦች ነው፣ከርሱ ውጭ ያለው ሁሉ የተዛባ ነው ማለት ነው?

- ሊሆን ይችላል፣እኔ ግን እንዲህ አላልኩም ! ቁርኣን ራሱ ብዙ ቦታ ላይ ለዐረቦች ብቻ ሳይሆን ለመላው የሰው ልጆች የተላለፈ መሆኑን ያመለክታል። ብዙዎቹ ትርጉሞቹ በጣም ጥሩ ሲሆኑ ልዩነቶች ሲያጋጥሙ ግን ማመሳከሪያው የዐረብኛ ቅጂው ብቻ ነው። የሚያስቀው ግን የዐረብኛው መጽሐፍ ከትውልድ ወደ ትውልድ የተላለፈው በጽሑፍ መልኩ ወይም በቃል በመወጣት ብቻ ሳይሆን፣የተለየ የአነባበብ ስልቱም ጭምር በድምጽ ከትውልድ ወደ ትውልድ የተላለፈ መሆኑ ነው።

- ለትርጉም ትክክለኛነት መመዘኛው ምንድነው?

- ተርጓሚው የሚተረጉመው የቁርኣንን ፍች እንጂ ቁርኣንን አይደለም። ቁርኣን በዐረብኛ ብቻ ነው ወደ ሌላ ቋንቋ የሚመለሰው ቁርኣኑ ሳይሆን ፍቺው ነው። ለማንኛውም ስታነበው ይህንን ትረዳለህ።

- ስለ ደከመኝ መታኛት፣ስለራበኝም እራት መብላት እሻለሁ። የአደም ነገርም ስለ አሳሰበኝ መረጋጋት፣ግራ ስለ ተጋባሁ ለካኽ ምላሽ መስጠትና ስለ ናፈቅኋት ፍቅሬንም ማግኘት እፈልጋለሁ። አንቺ ደግሞ የቁርኣን ትርጉሞችን በማንበብ ተጠምደሻል !

ካትሪና ፈገግ አለች፤በመሽኮርመም ቅላጼ እንዲህም አለች፦

- እንግዲያውስ በእራቱ እንጀምርና ከዚያ ፍቅሩን እናስከትል፤የተቀረውን ለሌላ ጊዜ እናቆይ።

ጆርጅ አማልዶ ከእንቅልፉ ተነሳና ወደ ሥራ ለመሄድ ተዘጋጀ። እየከበደውና ጥላቻ እየተሰማው ወጣ። ይህ ስሜት በካኽ ምክንያት ይሁን ወይም ገና እልባት ባላገኘለት የግራ መጋባት ሁኔታ? አያውቅም።
ወደ ቢሮው እንደገባ በቀጥታ ለአደም ደወለ። ሞይባይሉ አሁንም እንደ ተዘጋ ነው። አጭር የጽሑፍ መልክት ላከለት . . ከደቂቃዎች በኋላ ካኽ ደውሎ ወደ ቢሮው እንዲመጣ ጠየቀው . .

- የዓለምን ጣጣ ሁሉ በራስህ ላይ የተሸከምክ መሰልክ፣ምን ነክቶሃል?

- ምንም፣ትንሽ ድካም ተሰምቶኛል።

- ከፊትህ የሚነበበው ውጥረትስ !

- ምንም የለም፤ግን አንድ ውድ ወዳጄን አጥቼ እያፈላለኩት ነው፣መሰወሩ አሳስቦኝ ነው።

- በሥራ ቦታው፣በቤቱና በጓደኞቹም ዘንድ ፈልገሃል?

- አዎ፤የሚገርመው ነገር የካፌ የሥራ ባልደረባው አስተናጋጅ እንኳ ባልተለመደ ሁኔታ አለመምጣቱን ሳይናገር መቅረቱ ያስገረመው መሆኑ ነው።

- እህህ፣ውዱ ወዳጅህ ! አንተ ዘንድ ሆስፒታል ያገኘሁት አስተናጋጅ ነው? !

- አዎ።

- ከሆስፒታሉ ላባርረው ምንም አልቀረኝም ነበር፤እንዴት ከካፌ አስተናጋጅ ጋር ትወዳጃለህ? !

- እንዲያውም ካትሪና ነበረች ትእቢትህን ስታሳየው ልታባርርህ ምንም ያልቀራት። አደም ከወዳጆቼ ሁሉ ምርጡ ወዳጄ ነው፤ስለርሱ በዚህ ሁኔታ ስትናገር አያስደስተኝም።

- አንተ ለኩባንያው ዋና ሥራ አስፈጻሚ ለመሆን የታጨህ ሰው ነህ፤እንዴት ስለ አስተናጋጅ ጓደደኛ ትናገረኛለህ? በሥራ መስክ ሙያዊ ብቃትህ የላቀ ቢሆንም ማህበራዊ ብቃትህ ግን በጣም ደካማ እንዳይሆን ስጋት አለኝ። የሚያሳዝነው በከፍተኛ የኃላፊነት ቦታ ላይ ማህበራዊ ብቃትና ክህሎት ከሥራ ብቃትና ክህሎት የበለጠ አስፈላጊነት ያለው መሆኑ ነው።

- ማህበራዊ ንቁነትና ብቃት ሰዎችን በግርድፍ አስነዋሪ አቀራረብ በትእቢት ማናገር ነው? !

- ገቢህንና የሥራ ዕድልህን የሚያሰፉልህን ሰዎች የመያዝ ብቃትና ክህሎት እንዲኖርህ ማለት ነው።

- ወዳጅነት ለአንተ ዕድሎችን መፍጠር፣ሀብትና ገቢን መጨመር ነው?

- አዎ፣ወዳጅነት ብቻ ሳይሆን ሕይወትም በሁሉም ገጽታዋ እንደዚያ ነች። ይህ መቼ እንደሚገባህ ግን አላውቅም?

- ማወቁንም አልፈልግም።

- ወዳጄ አታክርር፣መቼ ነው የምትጓዘው?

- ባንተ ወዳጅነት አልኮራም፤የአደም ወዳጅነት ግን ለኔ ከምንም በላይ ምርጥ ወዳጅነት ነው።

- እህህ፣እኔን የሚያሳስበኝ ሥራህ እንጂ ወዳጅነትህ አይደለም፤መቼ ነው ወደ ስዊድን የምትጓዘው?

- ነገ መልስ እሰጥሃለሁ፤ፍቀድልኝ ልሂድ።

- የአይሮፕላን ትኬት ገዝተንልሃል፣ከሕዝብ ግንኙነት ሥራ አስፈጻሚው ከዊልያም መቀበል ትችላለህ . . እህህ፣ አስተናጋጁን ስታገኘው ግን የምስራቹን ንገረን።

ጆርጅ

ራሱን እየወቀሰ ወደ ቢሮው ተመለሰ። መርሁን እንደማይጥስና እንደማይጓዝ ለካኽ በቀጥታ ለመንገር
ለምን ድፍረት አነሰው?
ሥራውን እንዳያጣ ፍርሃት አድሮበት ይሆን? እንግዲያውስ እርሱም ያው እንደ ካኽ ገንዘብ ያስጨንቀዋል ግን ከመርህ ጀርባ ይደበቃል ማለት ነው
. .
ከርሱ ይልቅ ካኽ ለገዛ ራሱም ሆነ ለሌሎች ሰዎች ይበልጥ ግልጽ ነው ማለት ነው። ‹‹መርህን የሙጥኝ
የምንለው
ለግል
ጥቅማችን
የሚያገለግል
ሲሆን ከጥቅማችን ጋር ሲጻረር ግን እንጥሳለን›› ሲል እውነቱን ሳይሆን አይቀርም . . ወደ ካኽ ተመልሶ ያበጠው ይፈንዳ ውሳኔውን ለመንገር አሰበ፣ግና መለስ አለና ይይቅርታ ደብዳቤ ለመጻፍ ወሰነ . . በዚህ መሀል የሕዝብ ግንኙነት ኃላፊው ዊልያም ከተፍ አለ . .

- እንካ እነዚህ የአይሮፕላን ትኬቶች ከካኽ የተላኩ ናቸው።

- ፍላጎት ሳይኖረኝ እኔ እንድሄድ ካኽ እንዲህ ለምን እንደሚጓጓ በጣም ይገርመኛል . . እስከማውቀው ድረስ አንተ ወይም የሽያጭና ገበያ ሥራ አስኪያጁ እንዳትጓዙ የሚከለክል ነገር የለም፣እንዳውም በዋናነት የናንተ መደበኛ ሥራ እንጂ የኔ አይደለም !

- ተገዶ ነው እንጂ ራሱ ፈልጎት አይደለም።

- እንዴት? አልገባኝም !

- አንተ ቴል አቪቭ በነበርክበት ጊዜ የሥራ አመራር ቦርድ ወደ ዋና ሥራ አስፈጻሚነት ከፍ እንድትልና ካኽ ወደ ሌላ እህት ኩባንያ እንዲዛወር በስብሰባ ወስኖ ነበር። ካኽ ይህ ውሳኔ እንዲዘገይ ለማድረግ ሲል የዘየደው መላ ካንተ በስተቀር ሌላ ሰው ሊያከናውነው የማይችል ተልእኮ መኖሩን መንገርና ውሳኔው እስከዚያ እንዲቆይ ቦርዱን ማሳመን ነበር።

- እኔ ተልእኮውን የማልፈጽም ከሆነስ?

- እኔ እንጃ፤እኔ መሄድ እፈልግ ነበር ግን አልተቀበለም። ቲኬቶቹን ያዛቸው፣ቦታ የተያዘልህ ከዘጠኝ ቀን በኋላ ነው።

- አሁን ነገሮች ግልጽ እየሆኑልኝ ነው፤ለምን ችክ እንዳለ አሁን ተረዳሁ። የስዊድኑን ደንበኛ ስልክና አድራሻ ልትልክልኝ ትችላለህ?

- ከአምስት ደቂቃ በኋላ ኢሜይልህ ላይ ታገኘዋለህ።

- የሁሉም የሥራ አመራር ቦርድ አባላት ስልክና ኢሜይልም ላክልኝ።

- እልክልሃለሁ።

- ዊልያም አመሰግናለሁ።

ጆርጅ ደብዳቤውን መጻፍ ጀመረ፣አድራሻውን ለካኽ ማድረግ ትቶ ለሥራ አመራር ቦርድ አደረገው፦

‹‹የተከበራችሁ የሥራ አመራር ቦርድ አባላት

ለአስራ አራት ዓመታት ያህል የቆየሁበትን ኩባንያ በማገልገሌ ክብር ይሰማኛል። በኔ ላይ ለጣላችሁት እምነትም አክብሮቴ የላቀ ነው። ለዚህ የመታመን ደረጃ ተገቢው ሰው ሆኜ መገኘት ምኞቴ ነው። ኩባንያችንን ስኬታማ ማድረግ የሁላችንም ኃላፊነት ነው። ለኩባንያው ማበርከት የቻልኩትን እንዳበረክት ላስቻለኝ የዘውትር ድጋፋችሁ ያለኝን ከፍተኛ አክብሮትና ግምት እንድገልጽ ይፈቀድልኝ።

የሙያ ስነ ምግባሬንና የራሴን መርሆ የማልጥስ ከሆነ ከሥራ እንደምባረር ባልጠበቅሁት ሁኔታ ማስፈራሪያ ስለ ደረሰብኝ፣እናንተም ጥረቴን ግምት ውስጥ ታስገባላችሁ ብዬ በማሰብ የሥራ መልቀቂያ አቀርቤአለሁ። የሚገባኝ ሁሉ ተጣርቶ እንደሚሰጠኝም ተስፋ አደርጋለሁ። ሥራ መልቀቄ ለኔም ሆነ ለኩባንያው ስም ከመባረር የሚመረጥና መርሆዎቼንም በጥቅም ከመሸጥ የተሻለ ነው።

ላደረጋችሁልኝ ትብብርና መልካም አያያዝ ሁሉ ሁላችሁንም አመሰግናለሁ።

ጆርጅ ኒሶን››

ደብዳቤውን ጽፎ ሲጨርስ የተላከለትን የሥራ አመራር ቦርድ አባላትን አድራሻ ኢሜይሉ ላይ አገኘ። ካኽንም ጨምሮ ደብዳቤውን ለሁሉም የሥራ አመራር ቦርድ አባላት ላከላቸውና ወዲያውኑ ግቢውን ለቆ ወጣ . . ወደ አደም መኖሪያ ቤት ሄዶ ማንንም አላገኘም። ወደ ካፌው
አመራ፤እዚያም
አላገኘውም፤አስተናጋጅ ባልደረባውን ሲጠይቅ እንዲህ አለው፦

- አንተ ነበርክ ትናንት የመጣህ? ዛሬም አልመጣም፤ይሁን እንጂ አንድ ሰው ከአንድ ሰዓት ያህል በፊት ደውሎ የመኪና አደጋ ደርሶበት ሆስፒታል መሆኑንና ጤንነቱ በመሻሻል መሆኑን ነግሮናል።

ለውጥና ሽግግር (2)

ጆርጅ የሆስፒታሉን አድራሻ ጠይቆ በቀጥታ ወደዚያ ሄደ። እየሄደ ለካትሪና ደውሎ ነገራት . .

- ታምሜ ሆስፒታል ሳለሁ በአስገራሚ ሁኔታ ነበር ከጎኔ የቆመው፣እናም ውለታውን መመለስ ይኖርብኛል።

- በዚህ በኩል ብታልፍና አብረን ብንጠይቀው ምን ይመስለሃል?

- አሁን ወደ ሆስፒታሉ የተቃረብኩ ስለሆነ እኔ አሁን ልጎብኘውና አንቺ በማታው የሕሙማን መጠየቂ ጊዜ ልትጠይቂው ትችያለሸ።

ጆርጅ ወደ ሆስፒታሉ ደርሶ የአደምን ክፍል ጠይቆ ወደዚያ አመራ። ወደ ክፍሉ ሲገባ አደምን እግሩ ሙሉ በሙሉ በጄሶ ተጠቅልሎና ብዙ ሰዎች ከበውት አልጋው ላይ ተኝቶ አገኘው . .

- አደም እንዴት ነህ . . ወዳጄ ምን አገኘህ?

- እንደምነህ ጆርጅ፣አዝናለሁ የአጭር ጽሑፍ መልክትህን ከአምስት ደቂቃዎች በፊት ነው ሞባይሌ ላይ ያየሁት፤ስልኬ ገና አሁን ነው የመጣልኝ፤አንተ እንዴት ነህ?

- ምንድነው የተከሰተው?

- ደረጃ ስወጣ ወድቄ ቅልጥሜ ላይ ስብራት ደረሰ፤ትናንት ወደዚህ ሆስፒታል አምጥተውኝ የአጥንት ቀዶ ጥገና ተደርጎልኛል፣አሁን በጎ ነኝ።

- ለምን አልደወልክልኝም?

- ጆርጅ አንተ ታማኝ ወዳጅ ነህ፣አመሰግነሃለሁ። እውነቱን ለመናገር ለማንም መደወል በምችልበት ሁኔታ ላይ አልነበርኩም። ወደ ሆስፒታል የወሰደኝ ወዳጄ ነው ለሚያውቃቸው ለነዚህ ወዳጆቼ የደወለላቸው። ከነሱ ጋር ላስተዋውቅህ ፦ አሕመድ የኤሌክትሮኒክስ ኢንጂነር ከሶርያ፣አድሪያን ፋርማሲስት ከእንግሊዝ፣ዐሊይ የከፍተኛ ትምህርት የዩኒቨርሲቲ ተማሪ ከሰዑዲ ዐረቢያ፣ሸይኽ ባስም አልአዝሀሪ ከግብጽ የለንደኑ እስላማዊ ማዕከል ኢማም . . ከወዳጄ ከጆርጅ ጋር ላስተዋውቃችሁ የኮምፒውተር ሶፍትዌር ኢንጂነርና የተራቀቁ ሶፍትዌሮች ኩባንያ ምክትል ሥራ አስፈጻሚ ነው . . ያደናቃችሁትን ምርጥ ቦርሳ ያመጣልኝ እርሱ ነው።

- እንኳን ደህና መጣችሁ፣የወዳጄን ወዳጆች ለመጀመሪያ ጊዜ መተዋወቄ ነው

- ወዳጄ ጆርጅ ሥራ የሚበዛበትና ብዙ የሚጓጓዝ ሰው ነው።

- አደም እንዳላችሁ ቀደም ሲል የተራቀቁ ሶፍትዌሮች ኩባንያ ምክትል ሥራ አስፈጻሚ ነበርኩ፤ከአደም በጣም ብዙ ብዙ ነገር ተጠቅሜያለሁ።

- ቀደም ሲል? ! ከመቼ ወዲህ ነው ኩባንያውን የለቀከው?

- ከአንድ ሰዓት ያህል በፊት የሥራ መልቀቂያዬን አቅርቤ ነው ወዳንተ የመጣሁት።

- ለምን?

- ታሪኩ ረዥም ነው፣ይህን እንርሳውና . . እግርህ አሁን እንዴት ነው? ሐኪሙስ ምን አለ?

- እግዚአብሔር ይመስገን . . በጎ ነኝ አሁን የሕመም ስሜቱ ጋብ እያለ ነው። ለአምስት ቀናት እዚህ ለመቆየት የምገደድ ሲሆን ለአንድ ወር ያህልም እቤት ማረፍ ይኖርብኛል፣ከዚያም ለአንድ ወር ያህል በምርኩዝ ተደግፌ እንቀሳቀሳለሁ።

- ሸይኽ ባስም አልአዝሀሪ ፈገግ ብሎ ፦ ጭውውታችሁን ማቋረጥ አልሻም፣የዙህር (ቀትር) ሶላት ሰግደን እንድንመለስ ፍቀዱልን።

- እጠብቃችኋለሁ።

- ሸይኽ ባስም ከልጅነቴ ጀምሮ መምህሬና አስተማሪዬ ናቸው።

- ወዴት ነው የሄዱት?

- የቀትርን ጸሎት ለማድረስ ነው የሄዱት።

- ዛሬኮ ማክሰኞ ነው፣የምን ጸሎት ነው?

- እኛ ሙስሊሞች ነን፤ሙስሊሞች በየቀኑ አምስት ጊዜ ወቅቱን ጠብቀው ይሰግዳሉ፣ጸሎት ያደርሳሉ።

- ሙስሊም መሆንህን አወቅሁ፣ለኔ ግን ያልጠበቅኩት ዱብዳ ነበር ! አስቀድመህ ለምን አልነገርከኝም ነበር?!

- ነገሮችን አያይዘህና አገናኝተህ አትመለከታቸውም ብየህ አልነበረም? ስሜና ውይይቶቼ ብቻ ሳይሆን መልኬና ተክለ ሰውነቴ ሙስሊም ዐረብ መሆኔን በግልጽ ያመለክታሉ፣ዋናው ነገር ካንተ የሸሸግሁት ነገር የለም። ካቶሊካዊ ነህ? ፕሮቴስታንት ነህ? እያልክ በመውቀስ ስትጠይቀኝ የነበርከው አንተ ነህ። ሆን ብዬ የደብቅሁህ መስሎ ተሰምቶህ ከሆነ ግን ደጋግሜ ይቅርታ እጠይቃለሁ።

- በየቀኑ አምስት ጊዜ መስገድ አይደክማችሁም? !

- ሶላት ከዓለማዊ ሕይወት ልፋትና ከጣጣዎቿ እፎይታ ይሰጠናል፣አይደክመንም።

- እኛም አንደዚሁ በሳምንት አንድ ጊዜ በጸሎት እፎይታ እናገኛለን፣በቀን አምስት ጊዜ ግን አድካሚ ይመስለኛል !

- እኛ ግን በቀን አምስት ጊዜ ካልሰገድን ይደክመናል። የኛ ስግደት ብዙ ድካም የለበትም፣ወደ መሰጊድ መሄድ እንኳ ላያስፈልግ ይችላል።

- ወደ መስጊድ ትሄዳላችሁ?

- ወደ መስጊድ መሄድ ከተቻለ ተመራጭ ነው፣ካልተመቸ ግን በየትኛው ቦታ መስገድ ይቻላል፤እኔም ከአፍታ በኋላ በተሸከርካሪ ወንበሬ ላይ ሆኜ እሰገዳለሁ።

- በዚህ የሕመም ሁኔታ ላይ እያለህ ትሰግዳለህ?!

- አዎ፣እንዳውም በዚህ ሁኔታ ላይ መሆኔ የበለጠ ለጸሎት እንድገፋፋ ያደርጋል። ፈጣሪ አምላኬ ረድኤቱ ሁሌም ያስፈልገኛል፣አሁን ባለሁበት ሁኔታ ላይ ደግሞ አስፈላጊነቱ የበለጠ ነው። ይህ ባይሆን ኖሮ የሕይወት ፈተናዎች የሰውን ልጅ መከራን የመቋቋም አቅም አሳጥተው ከመልካም ስነ ምግባርና ከመርህ እንዲዛነፍ ያደርጉት ነበር።

- ይህ እውነት ነው . . ለመርህ ታማኝ መሆን አድካሚ ነገር ነው።

- ለዚህም ነው ሶላትና ከእግዚአብሔር ጋር ግንኙነት መፍጠር የሰውን ልጅ በትእግስትና በጽናት እንዲጎለብት የሚያደርግ የብርታትና የኃይል ምንጭ የሆነው።

- ቁርኣንን እንድታነቡ መልእክት ልኬላችሁ ነበር፣ለራሴ የትኛውን የቁርኣን ትርጉም እንደማነብ ግን አላውቅም።

- የዐረብኛ ቋንቋን አውቀህ እኛ የቁርኣንን ጥፍጥና እንደምናጣጥም አንተም እንድታጣጥመው ምኞቴ ነው። ለማንኛውም ሸይኽ ባስም ከተመለሱ በኋላ አንድ የትርጉም ቅጂ አበረክትልሃለሁ።

- እስላም የመጣው ለዐረቦች ብቻ ነው?

- ከምዕራቡ ዓለም ሌላ በዓለም ላይ የሚገኙ ሙስሊሞች ቁጥር በዐረብ አገሮች ከሚገኙት በብዙ እጥፍ ይበልጣል። እስላም አላህ ለነብዩ (ሰላም በርሳቸው ላይ ይወረድ) እንዳለው ሁሉ ለመላው የሰው ዘር የተለገሰ እዝነት ነው ፦ {(ሙሐመድ ሆይ !) ለዓለማት እዝነት አድርግን እንጂ አልላክንህም።} [አል አንቢያ፡107]

- እዝነት !

- አዎ እዝነት ነው፣በረከት ነው፣ጸጋ ነው . . ቁርኣንን ብታነበውና ብታጠናው ለዓለማት ሁሉ ምን ያህል እዝነትና ጸጋ እንደሆነ ልትደርስበት ትችላለህ።

- ካትሪና ስለ ካቶሊክ ስትናገር በምትናገረው ቃና ነው አንተም የምትናገረው።

- ካቶሊካዊነትን እንዳጠናህ ሁሉ . . እስላምን አጥናውና አሳማኝ ሆኖ ካላገኘኸው ወዲያ በለው።

- ላጠናወና ቁርኣንን በመቅራት ለመጀመርም ወስኛለሁ፤የማጠናው ግን በሂሳዊ መንገድ ነው።

- በጣም ጥሩና ተገቢም ነው። እስላም የዕውቀት ሃይማኖት ነው፤አስቀድመህ ሳታውቅና ሳትረዳው እንድታምንበት አይጠይቅህም። ለዚህም ነው ከቁርኣን መጀመሪያ ለነብዩ የተላለፈው ቃል ‹‹አንብብ›› የሚል የሆነው።

- በእስላም በጽኑ የምትተማመን ትመስላለህ . . ሮም ውስጥ ያገኘሁት አንድ ሙስሊም እንደኛ መሆንን እንደሚመኝ ነግሮኝ እስላምን እንዳላውቅ ነበር የመከረኝ።

- ከሙስሊሞች መካከል ‹‹እስላም የኋላ ቀርነትና የሽብርተኝነት ሃይማኖት ነው›› የሚልህም ሊያጋጥምህ ይችላል።

- ሰውየውም እንደዚያ ይል ነበር።

- ከሙስሊሞች መካከል እስላም ሴቶችን ስለመጨቆኑና እምነቱን እንዲቀበሉ ሰዎችን የሚያስገድድ ስለመሆኑ የሚናገርም ልታገኝ ትችላለህ።

- ሮም ውስጥ ያገኘሁት ሰው ያልከውን ሁሉ የሚናገር ነበር።

- የማቴማቲክስ፣የምህንድስና፣የሕክምና ወይም የኮምፒውተር ሳይንስን የሚራገምና የሚተች ሰው ሊያጋጥምህ ይችል የለም?!

- በጣም ብዙ ናቸው።

- ከነዚህ ሳይንሶች ደረጃ ምን የሚቀንሱት ነገር ይኖራል? ከሳይንሶቹ አስፈላጊነትና ጠቀሜታስ ምን ሊያጎድሉ ይችላሉ?

- በእርግጠኝነት ምንም አይኖርም፤ይሁን እንጂ እዚህ ላይ ነገሩ ትንሽ ለየት ይላል።

- በአስላም ላይ የተቀነባበረ የማጥላላት ዘመቻ ከመኖሩና በሳይንስ ላይ ይህን የመሰለ ዘመቻ ካለመኖሩ ውጭ ምንም ልዩነት መኖሩ አይታየኝም።

- የተቀነባበረ የማጥላላት ዘመቻ ስትል ምን ማለትህ ነው?

- ‹ሙስሊሞች› ያደረሱትን የለንደኑን የሽብር ጥቃት ታስታውሳለህ?

- አዎ፣በኋላ ላይ ግን ፍንዳታው የሙስሊሞች የሽብር ጥቃት አለመሆኑ ተረጋግጧል።

- ያ የተረጋገጠው ግን ሚዲያዎቹ ለረዥም ጊዜ ስለ ሙስሊሞች አሸባሪነት ሲያወሩ ከከረሙ በኋላ ነበር። ማስተባበያውን ግን እንደ ተለመደው አንድ ጊዜ በጨረፍታ አውርተው ነው ያለፉት። በዚያ ፍንዳታ ምክንያት እኔ ራሴ ተይዘው ከታሰሩት መካከል አንዱ መሆኔንስ ታውቃለህ? ወንጀሌ ሙስሊም መሆኔ ብቻ ነበር፣ሙስሊም ስለሆንኩ በቃ ሽብርተኛ ነኝ ማለት ነው። የተሰበሰቡት ማስረጃዎች ሙሉ በሙሉ ሙስሊሞች ከወንጀሉ ጋር ምንም ግንኙነት እንደ ሌላቸው እንዳረጋገጡስ ታውቃለህ? የሚያሳዝነው ግን የምዕራቡ ዓለም ሚዲያ ሙስሊሞችን ለመወንጀል ሁሌም በተጠንቀቅ ላይ መሆኑ ነው።

- ይህ የሚሆነው ሙስሊሞች በተደጋጋሚ በሚፈጽሙት ተግባር ምክንያት አይመስልህም?

- በሁሉም ማህበረሰቦችና በሁሉም ሃይማኖቶች ውስጥ ተስፈንጣሪዎች ይኖራሉ። ልዩነቱ ግን ከሙስሊሞች ጋር ያልተያያዘ ከሆነ ጉዳዩ እንደ ተራ ወንጀል ሲታይ፣ከነሱ ጋር ግንኙነት ካለው ግን የሽብር ወንጀል ተደርጎ መወሰዱ ነው ! ይህ አስቂኝ አይደለም?

- ለእስላም በጣም ስሜታዊ የሆንክ ወገንተኛ ትመስላለህ !

- ግልጽና ቀጥተኛ ልሆንልህና ሙስሊም እንዳትሆን ምንድነው የሚከለክልህ? ሰልመህ የመታደልን ሕይወት ለምን አትጎናጸፍም? !

- ያልጠበቅሁት ድንገተኛ ጥያቄ ነው፤መስለም ወይም እስላምን መቀበል እንዲሁ በቀላሉ የሚሆን ነው?!

- አዎ፣የቤተክርስቲያን ልዩ የጠመቃ ሥርዓት ወይም የአንዳንድ ሃይማኖቶች ዓይነት ውስብስብ ሂደት አያስፈልግህም፤በጣም ቀላል ነገር ግን ትልቅ ስር ነቀል ለወጥና ሽግግር ነው።

- አደም እስላምን ተቀብዬ የሚሰልም ይመስለሃል?

- አዎ፣እንዲያም እጅግ በጣም ቅርብ ነህ ብዬ ነው የማምነው።

- አደም ይቅርታ፣በሚገባ የምታውቀኝ አይመስለኝም። እኔ ከአእምሮዬ፣ከስነ አስተሳሰቤ፣ከእሳቤዬና ከመርሆዎቼ ጋር የማይጣጠምን ነገር የራሴ አድርጌ መያዝ የማልችል ሰው ነኝ።

- ይቅርታ . . እንዲያውም አንተ ነህ እስላምን የማታውቀው !

- ማለት የፈለከው አልገባኝም።

- ወደ እስላም መግባት በጣም ቀላል ነው፤ውስጥህ አሳማኝነቱን ሙሉ በሙሉ ከመቀበሉ በፊት ግን ወደ እስላም መግባት አትችልም። ተፈላጊው ነገር በአንደበት ‹‹ከአላህ በስተቀር በእውነት የሚመለክ ሌላ አምላክ አለመኖሩንና ሙሐመድ የአላህ መልእክተኛ መሆናቸውን እመሰክራለሁ›› ማለት ብቻ ሳይሆን ይህ ጽንሰ ሀሳብ አስቀድሞ በተጨባጭ እውስጥህ መስረጽ ነው። በመሆኑም ዋናው ነጥብ ከአፍአዊ ቅርጻዊ ጉዳዮች በፊት ከልብህ ውስጥ የተተከሉ እምነታዊ ጉዳዮች ናቸው ማለት ነው።

- አንድ ቀን ልሰልም እችላለሁ ብዬ ባላስብም የሚሆነውን ግን ማን ያውቃል? !

- እስላምን እንደምትቀበልና እንደምትሰልም ጽኑ እምነት ብኖረኝም ወደ እስላም መግቢያ በርህ ግን የሳይንስና የዕውቀት በር ነው የሚል ግንዛቤ አለኝ። ለዚህም ነው አንተ ሳይንስን፣ስነ አስተሳሰብን፣አእምሮንና መርህን የምትወድ በመሆንህ መጀመሪያ እስላምን ማወቅ አለብህ ከዚያ በኋላ ነው ሃይማኖቱን የምትቀበለው ብዬ የማምነው።

- በምትናገረው ነገር እኔን ወይም እስላምን ወይም ሁለቱንም? እያወደስክ እንደሆነ አላውቅም። ለማንኛውም ግን ሮም ውስጥ ያገኘነው ሙስሊም ‹‹ለኢየሱስ ያለኝ ታላቅ ፍቅር ወደ እስላም መራኝ›› የሚል መጽሐፍ ለካትሪና ከማበርከቱ በፊት የተናገረውንና ከዚህ ጋር ተቀራራቢ የሆነውን ነገር አስታወስከኝ።

- ሮም ላይ ያገኛችሁት ሙስሊም ቅድም እስላምን የሚያጣጥል ነው አላልከኝም ነበር?

- የሚያስገርመው ነገር ይኸኛው ሙስሊም ቅድም የነገርኩህ ሙስሊም ወንድም ነው፣ሁለቱንም አንድ ላይ ነበር ያገኘናቸው።

- ባንተ አስተያየት ማንኛቸው ነው የሚሻለው?

- እኔ እንጃ፣የመጀመሪያው ታላቅ ሲሆን ሁለተኛውና ታናሹ ግን ለአባትና እናቱ የበለጠ አክብሮት አለው፣እነሱም በጣም ያከብሩታል። ሁለቱን ማነጻጸር አላሳሰበኝም።

- ካትሪና መጽሐፉን አነበበች?

- አዎ፣ያውም ሁለቴ ነው ያነበበችው፤ከውስጥ እንደ አንቀጠቀጣትም አውቃለሁ።

- አንተስ አንብበሃል?

- አዎ አንብቤአለሁ፤አንተ ግን በቁርኣን እንድጀምርና ትርጉሙን አንደምታበረክትልኝ ነበር የነገርከኝ።

- እነ ሸይኽ ባስም ገና እየሰገዱ ነው መሰለኝ ትንሽ ዘገዩ፣አሁን ይመጣሉ። ፍቀድልኝና አሁን እኔም ልስገድ . . ስለ እስላም መጠየቅ ከፈለግህ ሸይኽ ባስም ሊቅ ናቸው፣እኔ የርሳቸው ተራ ተማሪ ነኝ። ላንተ ያበረከትኩልህ የቁርኣን ትርጉም መጽሐፍም ሸይኽ ባስም ዘንድ ነው።

- ከመጡ ጸሎትህን አድርሰህ እስክታበቃ እጠብቀሃለሁ፣አለዚያ እሄዳለሁ ፍቀድልኝ።

- መልካም።

ጆርጅ በአትኩሮት እየተመለከተው አደም ‹‹አላሁ አክበር›› ብሎ ሶላቱን ጀመረ። በዚህ ወቅት ሸይኽ ባስምና ባልደረቦቻቸው ደረሱ . . ጆርጅ ፊቱን ወደነሱ አዞረ . .

- የእስላም ሃይማኖት መሪ መሆንዎንና ያበረከተልኝን የቁርኣን መጽሐፍ ትርጉም ከርስዎ እንደምቀበል ነግሮኛል።

- እስላም ውስጥ የሃይማኖት መሪዎች የሚባል የካህናት ዓይነት መደብ የለም። መጽሐፉ ውጭ መኪና ውስጥ ነው ያለው፣አብረን ሄደን ብሰጥህ ምን ይመስለሃል?

- መልካም . . ብዙ ስለ ዘገየሁ መሄድ ይኖርብኛል፣የማይረዝም ካልሆነ ግን አደም ጸሎቱን እስኪጨርስ እንጠብቅ።

- ሶላታችን እንደ ሃይማኖታችን ሁሉ ገርና ቀለል ያለ ነው፣ሁለመናው መታደል ነው፣ደስታ ነው።

- መታደል ነው፣ደስታ ነው? !

- አዎ . . የዛሬው ዓለማዊ ሕይወትና የወዳኛው ዘላለማዊ ሕይወት ተድላና ደስታ ነው። የአደም ወዳጅ ሆነህ ይህን ሳይነግርህ መቅረቱ የሚገርም ነው። ወዳጅህ ሆኖ ይህን ታላቅ ሃይማኖት ሳያስተዋውቅህ በመቅረቱ አደምን እወቅሰዋለሁ፣እስላምን ከማስተማር የተሻለ የሚያበረክትልህ ምንም ክቡር ስጦታ የለም። ብዙዎቹ የሰው ልጆች ለመንፈሳዊና ዓለማዊ ሕይወታቸው የሚበጀውን ለመፈለግ በጥመትና በጥፋት መንገዶች ውስጥ ሲዳክሩ የአላህ ነብያትና መልክተኞች መደምደሚያ የሆኑትን ነብይ ሃይማኖት እንዴት ችላ እንዳሉ አታይም?

- ምናልባት እርስዎ ዘንድ ያለውን የቁርኣን ትርጉም መጽሐፍ ያበረከተልኝ ለዚህ ሊሆን ይችላል።

አደም ሶላቱን አብቅቶ ወደ ጆርጅና ሸይኽ ባስም ፊቱን አዞረ . .

- ሸይኽ ባስም አይውቀሱኝ፣እስላም የዛሬው ዓለም ሕይወትና የመጪው ዘላለማዊ ዓለም ሕይወት ተድላ መሆኑን ነግሬዋለሁ . .

ሸይኽ ባስም ፈገግ እያለ፦

- ጆርጅ እኛ ከያንዳንዱ ሶላት በኋላ የሕይወትን ሸክምና ጣጣ፣ ቻይ፣ቸር፣ርህሩህ፣ሰሚ ውስጠ ዐዋቂ በሆነው ፈታሪ ጌታ ላይ ስንጥል በዓለም ላይ ወደር የሌለው ደስታ ይሰማናል።

- ጆርጅ ሸይኽ ባስም የጠቀሱትን በዛሬው ዓለም ሕይወትና በመጪው ዘላለማዊ ዓለም ሕይወት መታደልን እመኝልሃለሁ።

- ተምሬ አውቄው አሳማኝ ሆኖ ካገኘሁትና በጥልቅ ሂሳዊ ምርምር ካጠናሁት በኋላ እንጂ ሃይማኖቴን መቀየር አልችልም። አደም በሁሉም ሃይማኖቶች ላይ በዚህ መንገድ አይደለም ጥናት ያካሄድኩት?

- ልክ ነው፤የኔ ጥያቄም በዚያው ተመሳሳይ መንገድ እንድትቀጥል ነው፤እንድትሰልም ብጓጓም እስላም ግን ማወቅ ቀዳሚ መሆኑን ያስተምረናል።

- መጀመሪያ ማወቅና መማር አለብህ፤ወዳጄ ከዚያ በኋላ ካልሰለምክ ግን ማመካኛ አይኖርህም። አሁን እንሂድ?

- ካወቅኩት እስልምናን እንደምቀበል ያላችሁ ይህ ሁሉ በራስ የመተማመን መንፈስ ምንጩ ምን እንደ ሆነ አላውቅም።

- ምንጩ ከአላህ ዘንድ በመጣው እስላም ላይ ያለን ፍጹማዊ መተማመን ነው።

- እንግዲያውስ አየዋለሁ ! ! ቁርኣንን ለማንበብ ቃል እገባላችኋለሁ። ስለ እስላም ለማወቅ አነባለሁ፣እወያያለሁ፣በጥልቀት እመረምራለሁም። ከዚያ በኋላ እወስናለሁ።

- ግሩም ድንቅ ነው . . ተመራጩም ይኸው ነው።

- ሌሎች ሃይማኖቶችን ለማወቅ እንደተጓዝክ ሁሉ እስላምን ለማወቅና ለመመርመር መጓዝን አትርሳ።

- አሁን እንሂድ . . መጽሐፍ ቅዱሳችሁን አነባለሁ፤ከዚያ የሚሆነው ይሆናል። አሁን ሥራ አልባ ሆኛለሁና ነገ ተመልሼ ልጠይቅህ እሞክራለሁ።

- ሥራውን መልቀቅህ ግን አስደንግጦኛል። የተቻኮልክ ትመስላለህና ነገ ካልመጣህ ስልክ እንደዋወል፤ፈጣሪ ካንተ ጋር ይሁን።

ጆርጅ የቁርኣንን ትርጉም ይዞ ወደ ቤቱ ተመለሰ። ካትሪናን እቤት አላገኛትም፤ደወለላትና አደምን ለመጠየቅ ወደ ሆስፒታሉ በመሄድ ላይ መሆኗን ነገረችው . . የቁርኣን ንባቡን ለመጀመር ወሰነ። ከአደም በኩል የተቸረው ድንቅ አቀባበልና አያየዝ አስገርሞታል፣በተለይም እስላምን ከሚያስተዋውቁ ሌሎች መጽሐፎች ይልቅ በቁርኣን እንዲጀምር ማድረጉ። ከሁለት ሰዓት ያህል በኋላ ካትሪና ወደ ቤት መለሰች . .

- አደምን ጠይቄ መመለሴ ነው።

- የኔ ወዳጅ በመሆኑና እኔን ለማስደስት ብለሽ እንጂ እንዳልሄድሽ አውቃለሁ።

- ግን በጣም የሚገርም ሰው ነው !

- እንዴት?

- እኔ እንጃ፣እርሱም ሆነ አብረውት ያሉ ሙስሊሞች ሁሉ ሴቶችን አይጨብጡም፣በትህትና ይቅርታ ይጠይቃሉ። በአይዶች ወይም በክርስትያኖች ዘንድ ያለው ዓይነት በሴቶች ላይ የሚፈጸም መድልኦ ይሆን?

- ሊሆን ይችላል . . እኔ እንጃ። እኔ ከሁለት ሰዓት በፊት ስለ እስላም ማንበቤን በመጽሐፍ ቅዱሳቸው በቁርኣን ጀምሬአለሁ። እውነቱን ለመናገር እስካሁን ያነበብኩት ሴትን በፍትሐዊነት የሚመለከታትና አክብሮት የሚቸራት መሆኑን ነው።

- ልክ ነህ . . የቁርኣንን ትርጉም አንብቤያለሁ፤እንዳልከው ነው፤ያስገረመኝ ግን ያሳዩኝ አያያዝ ነው !

- ለምን ? ያስተዋልሽው አንቺን የማዋረድ ወይም የማንቋሸሽ ሁኔታ ነበር?

- ፈጽሞ አልነበረም፤እንዲያውም በጣም ትሁቶችና ተግባቢዎች ናቸው፣ግን አልጨበጡኝም፣ወደኔም አልተመለከቱም።

- ግን ትንሽ ቆይተሻል፣ሀሳብ አልተለዋወጣችሁም?

- ብዙ ተወያይተናል፤የምናገሩት በአብዛኛው ስለ እስላም ነው። አንዳንድ ቀሳውስትን እንዳስታውስ ለምን እንዳደረጉኝ አላውቅም።

- ምናልባት ባልደረባው ባስም የሃይማኖት መሪ ስለሆነ ይሆናል።

- አይደለም፣ባስም የሃይማኖት መሪ አይደለም፣ይህን አገላለጽም አይቀበልም። እስላም ውስጥ እናንተ ዘንድ እንዳለው ዓይነት የጵጵስና ሥርዓትና የሃማኖት መሪዎች የሚባል የካህናት መደብ የለም። ለማንኛውም ግን እርሱ የሃይማኖት እውቀት ያለው ምሁር ነው።

- አዎ . . ልክ ነሽ፤እርሱም ያለኝ ይህንኑ ነው፤ፈገግታ የማይለየው ትሁት አመለ ሸጋ ሰው ነው። እንዳንቆራረጥ ቢዝነስ ካርዱን ሰጥቶኛል። ታውቂያለሽ ሙስሊም እንድሆን ይፈልጋል ! ! ያላቸው በራስ መተማመን በእጅጉ ይገርመኛል !

- ካትሪና የሆነ ነገር ከትውስታ መዝገቧ ታነብ ይመስል ጣሪያ ጣሪያውን ተመለከተችና ፦ እንደ መነኮሳት ሙሉ ጊዜአቸውን ለአምልኮ የሚያውሉ ባይሆኑም ሁሉም ሰናይ ምግባር ያላቸውና አምልኮተ እግዚአብሔርን የሚያበዙ ናቸው። የሚያስደንቀው ነገር ሥራቸውንም ሆነ ትምህርታቸውን አምልኮ አድርገው ይመለከታሉ፤እኛ ዘንድ እንዳለው ዓይነት ሕይወትን ከአምልኮተ እግዚአብሔር ነጥለው አይመለከቱም። ታቂያለሽ አደም አልጋው ላይ ሆኖ የጸሎት ሥርዓቱን አከናውኖ ‹‹እኛ በሁሉም ስፍራ እንጸልያን፣ሃይማኖት ገር ነው›› አለኝ።

- እኔ እያለሁም ሰግዶ በቀን አምስት ጊዜ እንደሚሰግዱና ስግደታቸው ተድላና ደስታ እንደሚያጎናጽፋቸው ነው የነገረኝ። ከፍተኛ በሆነ በራስ የመተማመን ስሜት የሚናገሩት ቢሆንም ያሉት ነገር አላሳመነኝም።

- እውነት ነው . . ያላቸው በራስ የመተማመን ደረጃ በጣም ከፍ ያለ ነው፤ንግግራቸውም ትልቅ ተጽእኖ የሚያሳድር ነው። ለሰው ያላቸው አያያዝ፣ፈግገታቸውና ተግባቢነታቸውም ወደር የለውም።

- በአድናቆታቸው የተያዝሽ ትመስያለሽ !

- ጉዳዩ የማድነቅ አለማድነቅ አይደለም፤ዋናው ጉዳይ ሙስሊሞች፣ቁርኣንና እስላም እኔ ከለመድኩት ሙሉ በሙሉ የተለየ ሥርዓትና ተፈጥሮ መሆኑ ነው።

- ይበልጥ አብራሪው፤መጽሐፍ ቅዳሳቸውን ቁርኣንን ማንበብ ስጀምር ተመሳሳይ ስሜት ነው የተሰማኝ። በተሟላ ሁኔታ ምንነቱን ያልተረዳሁትን እንግዳ ስሜት ነው እውስጤ የፈጠረው። በተለይም የእግዚአብሔርን አንድነት፣እርሱን ማላቅና ማክበር፣ስሞቹንና ባህርያቱን በመሳሰሉት ርእሰ ጉዳዮችም ሆነ የነብያትን ታሪኮች በተለይም የኢየሱስንና የማርምን ታሪክ የሚመለከቱ ወይም ሞራልና ስነ ምግባርን የሚዳስሱ ጉዳዮች ልቤን ነክተዋል።

- እኔም ተመሳሳይ ስሜት ነው ያሳደረብኝ፣ግና ለመወሰን መቸኮል የለብንም የሚል አስተያየት አለኝ። ስለ ሃይማኖቱ ያለን ዕውቀት በጨመረ ቁጥር ነገሮች ግልጽ እየሆኑ ይሄዳሉ፣ደካማ ጎኑን፣እንከኑንና እርስ በርስ መጣረሱን ማወቅ እንችላለን። እንዲህ ያሉ ነገሮች እስላም ውስጥ ስለመኖራቸው ከኋላ ቀርና አምባገነናዊ የሙስሊሞች አገዛዝ ሁኔታ የበለጠ ማስረጃ አይኖርም።

- ለአደም ትልቅ አድናቆት ቢኖረኝም፣ከአፍታ በፊት ቁርኣንን ሳነብ የሆነ ዓይነት እርካታ የተሰማኝ ከመሆኑም ጋር፣እስላምን የማወቅ ብርቱ ፍላጎት ያለኝ መስሎ አይታየኝም። ይሁን እንጂ ለማወቅ ከራሴ ጋር እታገላለሁ።

- አውነቱን ለመናገር መጽሐፍ ቅዱሳቸውን ማንበብ የተለየ ስሜት ይፈጥራል !

- የምሥራች ልበልሽ . . ዛሬ የሥራ መልቀቂያዬን አቅርቤያለሁ። መሰሪውን ውሸታም ካኽን አምርሬ ነው የምጠላው። የተሰጠኝን የሥራ ዕድገት ከኔ ሸሽጎ ወደ ስዊድን እንድሄድ ነው የመደበኝ። መልቀቂያውን ያቀረብኩት የሥራ አመራር ቦርዱን በሚያነሳሳ መንገድ ነው፤ምላሽ ካልሰጡኝ የመጨረሻው መልቀቂያ ይሆናል።

- እናም መርሆዎችህ በፍላጎትህና በጥቅሞችህ ላይ ድል ተቀዳጅተዋል ማለት ነው?

- ሊሆን ይችላል፤ግን ደሞ ለውሳኔ የገፋፋኝ የሥራ አመራር ቦርዱን ውሳኔና ካኽ የወሰደውን አቋም ማወቄ ሊሆን ይችላል። ተስፋ የማደርገው ተገቢ የሆነ አቋም ይወስዳሉ ብዬ ነው። ለማንኛውም ግን ገንቢ ያልሆነ ምላሽ ከነርሱ ካላገኘሁ ጉዳዩን ወደ ሠራተኞች ማህበር እወስዳለሁ።

- እኔ ግን አሁንም በመርሆዬና በሥራዬ መካከል ሆኜ እየታገልኩ ነኝ . . ጥርጣሬዬን ሸፋፍኜ እሸሽ ነበር፣አንተ ነህ የተሸፋፈነው ሁሉ ይፋ ካልወጣ ብለህ የጸናህ።

- ከተጋባንበት ጊዜ ጀምሮ በዚህ በመጨረሻው ወር እንዳደረግሽው ፈጣን ለውጥና ሽግግር ስታደርጊ አይቼ አላውቅም፣በተለይም ከቴል አቪቭ ከተመለስኩ በኋላ !

- ለውጥና ሽግግር ሙሉ በሙሉ ክፉ ወይም ሙሉ በሙሉ በጎ አይደሉም፤የኔ መለወጥና ሽግግር ወደ በጎው እንዲሆን እመኛለሁ።

- እህህ፣ከካቶሊካዊነት የተሻለ በጎ ይኖራል?

- በመድኃኒታችን በኢየሱስ ያለኝ እምነት እጅግ በጣም ጽኑ ነው፣በካቶሊካዊነት ላይም እንዲሁ ነው፣ከርሱ የተሻለ አለ ብዬ አልገምትም፣ግን ማን ያውቃል? !

- እህህ፣ዛሬ በጊዜ መተኛት እፈልጋለሁ፣ሆኖም የኢሜይል መልክቶችን በፍጥነት አነባለሁ።

ጆርጅ ኢሜይሉን ከፈተ፤መርህን አስመልክቶ ልኮ ለነበረው መልክት አንዳንድ መልሶችን አገኘ። ሁሉንም አንድ ላይ ጠቅለል አድርጎ መልሶ ለሁሉም ላከላቸው። የሁሉም እርሱ ከደረሰበት ውሳኔ ጋር ከሞላ ጎደል ተመሳሳይ ነበር።

‹‹ጃኖልካ በቂ ድፍረት ላለው ሰው ያለ ጥርጥር መርህ ቀዳሚ ነው፤ግና ችግርና ድካም አለው።

ሌቪ ትክክለኛው ነገር መርህ ይበልጥ አስፈላጊ መሆኑ ነው። የኑሮ ጫናን የመቋቋም አቅም ስለሚያንሰን የግድ ሁላችንም ማድረግ እንችላለን ማለት ግን አይደለም።

ሐቢብመርህን ነው የምናስቀድመው፣አለዚያማ ወደ ዱር አውሬነት ተለወጥን ማለት ነው።

ካትሪናመርህ ይቀድማል ተብሎ ነው የሚጠበቀው፣ ነገር ግን አስቸጋሪ ውሳኔ ነው።

ቀደም ሲል በቁርኣን ዙሪያ ለላኩላችሁ መልክት ምላሻችሁን በመጠባበቅ ላይ ነኝ።

ጆርጅ››

ኢሜይሉን ማየት ቀጥሎ ከጃኖልካ የተላከ መልእክት አገኘ . .

‹‹ወዳጄ ጆርጅ . .

ከተዋወቅን አጭር ጊዜ ቢሆንም በአመለካከት መቀራረብ ብቻ ሳይሆን በመካከላችን መመሳሰል መኖሩን ነው የተገነዘብኩት። ሰለዚህም ምናልባት ሊያስገርምህ በሚችል ጉዳይ ላይ ላማክርህ ወደድኩ።

እናንተ ከሄዳችሁ በኋላ ሙስሊሙ ሰውየ ለባለቤትህ የሰጣትን መጽሐፍ ከኢንተርኔት ላይ አግኝቼ አነበብኩ። ከዚያም የሕንጻ ዲዛይን ኢንጂነሩን ሙስሊም አግኝቼ ስወያይ መጀመሪያ የቁርኣንን ትርጉም እንዳነብ ጠየቀኝና ከአንድ ጊዜ በላይ ሙሉውን አነበብኩ። ከንባቤ በኋላ እንደገና ተገናኝተን ሀሳብ የተለዋወጥን ሲሆን ይህ መጽሐፍ ምን ዓይነት ምትሃት እንዳለው አላውቅም ! ስለ እስላም ዝርዝር ጉዳዮችን ጠይቄው ጥልቀት ያለው ዕውቀት የሌለው መሀንዲስ ብቻ መሆኑን ነገረኝ። ማን በዝርዝር ሊያስረዳኝ እንደሚችል ሲጠይቀው እንግዳ በመሆኑ ጣሊያን ውስጥ ይህን ማድረግ ማን እንደሚችል እንደማያውቅ አስረድቶኝ ስለ እስላም የበለጠ ለማወቅ ከፈለግሁ ሁለት መንገዶች እንዳሉ ጠቆመኝስለ እስላም የተጻፈውንና የተሰራጨውን ማንበብ መስማትና ማየት ሲሆን፣ይህም በቁጥር የበዛ ቢሆንም ከፊሉ በእስላም ጠላቶች የተጻፈ ነው። ሌላው መንገድ ጣሊያን ውስጥ የሚኖርና እስላምን በጥልቀት የሚያውቅ ሰው መፈለግ አለዚያም መሳፈር ነው። እናም ሁለቱንም መንገድ ወስኜ እናንተ ከሄዳችሁበት ጊዜ ጀምሮ በየቀኑ ከአምስት ሰዓት ላላነሰ ጊዜ ስለ እስላም በማንበብ ላይ እገኛለሁ። በቅርቡ ወደ ግብጽ ወይም ወደ ሊብያ ለመጓዝ እፈልጋለሁ። ምን ትመክረኛለህ?

ሰላምታዬ ላንተና ለካትሪና ይድረስ

ጃኖልካ››

መልስ ጻፈለት . .

‹‹ወዳጄ ጃኖልካ

ደብዳቤህን አንብቤ ድፍረትህና ጀግንነትህ በእጅጉ አስደንቆኛል። እኛ ከሄድን በኋላ በአጭር ጊዜ ውስጥ ደያረግከው ለውጥና ሽግግር ከፍተኛና ከጠበቅኩት በላይ ነው። ሁለቱንም መንገዶች መከተልህን እደግፋለሁ። የደረስክበትን ውጤት እንድታሳውቀኝ እፈልጋለሁ፣ባንተና በንቁ ተመራማሪ አእምሮህ ብዙ እጠቀማለሁ።

ሰላምታዬ ይድረስህ

ጆርጅ››

ለውጥና ሽግግር (3)

ጆርጅ ከእንቅልፉ ሲነቃ ካትሪና ቁርስ አዘጋጅታ

ነበር . . አብረው
ቁርሱን በሉ . .

- ዛሬ ሥራ የለኝም፣ምን እንደማደርግ አላውቅም።

- ለሥራ መልቀቂያ ጥያቄህ ምላሽ ያልመጣ ስለሆነ መቅረትህ በሠራተኛ ማህበሩ ዘንድ ማስረጃ እንዳይሆንብህ ወደ ሥራ ሂድ።

- ይህን አላሰብኩም ነበር፣እውነትሽን ነው።

- አንተ እንኳ ቁርጥ አድርገህ ወስነሃል፤እኔም የራሴን ቀርጥ ያለ ውሳኔ ዛሬ ለመወሰን እሞክራለሁ።

- ቁርጥ ያለ ውሳኔ ! . . እንዴትና በምን?

- እኔ እንጃ፣ግን እሄድና ነገሩን ለመወሰን እሞክራለሁ።

- ትናንት በመርህና በጥቅም መካከል ያለውን ግጭት አስመልክቶ የተላከለኝን ማጠቃላያ ልኬልሻለሁ፤ውሳኔ ላይ ለመድረስ ምናልባት ሊረዳሽ ይችላልና አንቢቢው።

- ከመወሰኔ በፊት አነበዋለሁ። እንዳይረፍድብኝ አሁን ልሂድ።

- እኔም አሁን ልሂድ።

ጆርጅ ወደ ሥራው አመራ፤ወደ ቢሮው እንደገባ የሕዝብ ግንኙነት ኃላፊው በንዴት ገንፍሎ መጣ ፦

- ምንድነው ያደረከው?!

- ምንም አላደረግኩም፣ምን ተፈጠረ? !

- ትናንት አንተ ከሄድክ በኋላ ካኽ እሳት ለብሶ እሳት ጎርሶ አስጠራኝ። ለመጀመሪያ ጊዜ ነው እንዲህ ተናዶ ያየሁት። ጆርጅ የሥራ አመራር ቦርድ አባላትን አድራሻ ከየት አገኘ? ብሎ አፋጠጠኝ፤አላውቅም አልኩት።

- እኔ ሰጠሁት ለምን አላልክም?!

- ሊያጠቃኝ ቢፈልግስ ብዬ ሰጋሁ ! ከግል ጥቅሙ ውጭ ምንም የማይታየው ግፈኛ መሆኑን መቼም ታውቃለህ።

- እንዲህ ነው እንግዲህ እርስ በርሳችን የምንፈራራው . . በጣም የሚገርም ነው . . የተቆጣበትን ምክንያት ግን ታውቃለህ?

- እንደሚመስለኝ የሥራ አመራር ቦርድ አባላቱ በአንተ ደብዳቤ ላይ ለመነጋገር በሦስት ቀናት ውስጥ አስቸኳይ ስብሰባ እንዲደረግ ደውለው ጠይቀውታል።

- ለምንድነው የሚሰበሰቡት?

- እኔ እንጃ፣የማውቀው ነገር ጉዳዩ ካንተ ጋር የተያያዘ መሆኑን ብቻ ነው። ለዚህ ነው የጻፍከውን ደብዳቤ ይዘት የጠየቅሁህ?

- እናም ነገሩ በጣም አበረታች ነው ማለት ነው፣ይህን አልጠበቅሁም ነበር !

- አበረታች ! ምኑ ነው አበረታቹ?!

- ምንም አይደለም፣የሥራ መልቀቂያ ደብዳቤ ነው የላኩላቸው። ለማንኛውም አድራሻዎቹን አንተ እንደ ሰጠኸኝ አንድም ሰው እንደማያውቅ እርግጠኛ መሆን ትችላለህ።

- አመሰግናለሁ . . ፍቀድልኝ ልሄድ።

ጆርጅ
በቀጣይ
የሚወስደው
እርምጃ
ምን
መሆን
እንዳለበት በማሰላሰል ተጠመደ። የካኽን የማታለልና የመዋሸት ስልቶች አሳምሮ ያውቃል። ኩባንያውን መተው ስለማይፈልግ ስልቶቹን በቀላሉ በሥራ አመራር ቦርዱ ስብሰባ ላይ ሊጠቀምበት ይችላል፤በቦርዱ ስብሰባ ላይ ለመሳተፍ ይጠይቃል ወይስ ዝርዝር መረጃዎችን ያቀርብላቸዋል? ምን ያድርግ? የሚገርመው ደግሞ ከሥራ አመራር ቦርድ አባላት መካከል እስካሁን ድረስ መልስ የሰጠው ሰው የለም! በመሆኑም የሚሰሙት ከካኽ ሊሆን ነው፣ይህ ፈጽሞ የማይፈልገው ነገር ነው። ቆም ብሎ አሰበበትና ለሥራ አመራር ቦርዱ በድጋሚ ደብዳቤ ለመጻፍ ወሰነ፦

‹‹የተከበራችሁ የሥራ አመራር ቦርድ አባላት

አስራ አራት ዓመታት የቆየሁበትን ኩባንያ በማገልገሌ ኩራት ይሰማኛል። በኔ ላይ የጣላችሁት እምነትም ለኔ የኩራት ምንጭ ሲሆን ለዚህ ተገቢው ሰው ሆኜ መገኘትም ምኞቴ ነው። ኩባንያችንን ወደፊት ማራመድ የሁላችንም ኃላፊነት መሆን ይገባል። ማስመዝገብ የቻልኩትን ስኬት እንዳስመዘግብ ያደረገኝ የናንተ ድጋፍና ትብብር በመሆኑ ለዚህ ያለኝን አድናቆትና ምስጋና እንድገልጽ ይፈቀድልኝ።

በደሌን በመንገር የሥራ መልቀቂያ ያቀረብኩላችሁ ቢሆንም ከናንተ ያገኘሁት መልስ የለም። ይህ በደሌ እንደ ቀጠለ የሥራ መልቀቂያው ተቀባይነት አግኝቷል ማለት ነው? ወይስ ፍትሕ አግኝቼ ሥራዬን እቀጥላለሁ ማለት ነው? ከሥራ አመራር ቦርዱ ጋር በቀጥታ የመወያየት ዕድል እንደሚሰጠኝ ተስፋዬ የጠበቀ ነው።

ለመልካም ትብበራችሁና ለቀና አስተያየታችሁ ሁላችሁንም አመሰግናለሁ።

ጆርጅ››

በዚህ ደብዳቤ ማስተላለፍ የፈለገው በሥራ አመራር ቦርድ ስብሰባ ላይ ተገኝቶ ሁሉንም ነገር በግልጽ የማቀረብ ፍላጎቱን ነበር። ይሁን እንጂ ደብዳቤውን እንደላከ ወዲያውኑ የቢሮ ስልኩ አቃጨለ፤ደዋዩ ካኽ ነበር . .

- ባለ መርሁ ይህ ሁሉ ለመርህ ሲባል ነው ! አሁን ወደ ቢሮዬ መምጣት ትችላለህ?

- አዎ ለመርሆዬ ብዬ ነው፣ፈጽሞ በመርሆዬ ላይ አልደራደርም።

- አሁን ወደኔ መምጣት ትችላለህ?

- አዎ አሁን እመጣለሁ።

ጆርጅ ወደ ቢሮ ሲደርስ ካኽን ተቆጥቶ

አገኘው . . በነገር ተቀበለው . .

- ጆርጅ ምንድነው የፈለከው?

- መርሆዬን አለመጣስ ነው የፈለኩት።

- የኩባንያው ዋና ሥራ አስኪያጅ መሆን የፈለግህ ትመስላለህ።

- ለመሆን አልጓጓሁም፣ከመጣ ግን ብቁና ተገቢው ሰው ስለሆንኩ ችግር የለውም።

- እናም ጉዳዩ የመርህ ጥያቄ ሳይሆን የሥልጣን ጥያቄ ነው ማለት ነው።

- እንዳሻህ መረዳት ትችላለህ፤ለማንኛውም ግን እኔ መርሆዬን አልጥስም። የመጣሁት ደግሞ አንተ ስለጠየከኝና እንስማማለን ስላልክ ብቻ ነው። ካኽ እርግጠኛ ሁን እኔ መርሆዬን ፈጽሞ መጣስ አልችልም።

- ጉዳዩ የስልጣን ሳይሆን አንተ እንደምትለው የመርህ ከሆነ የማቀርብልህ ሌላ ሀሳብ አለኝ።

- ምንድነው?

- እኔ ወደ ስዊድን እጓዛለሁ፣ግን አንተ ከለንደን ወደሆነ ቦታ የመሄድ ግዴታ ይኖርብሃል።

- ለምን?!

- ነገሩ ከራሴ የግል ጉዳይ ጋር የተያያዘ ነው። እኔ በዚህ ወቅት ኩባንያውን ለቅቄ ወደ ሌላ መዛወር አልፈልግም፤አንተ ለንደን ውስጥ ሆነህ የሥራ አመራር ቦርዱ ከተሰበሰበ ግን ለኔ እድገት ሰጥቶ ይህን ኩባንያ ለቅቄ ወደ ሌላ እንድዛወር ይወስናል። ለዚህ ነው ያንተን የስዊድን ጉዞ አስፈላጊነት ያሳመንኳቸው፤(ፈገግ ብሎ ቀጠለና) ፦ ስሜትህን ለመጠበቅና መርሆህን ለማክበር ስል እኔ እጓዛለሁ፣አንተ ግን ውሳኔ መዘግየት እንዲችል በዚህ ጊዜ ከለንደን ውጭ መሆን ይኖርብሃል።

- ወዴት ነው የምሄደው?

- ወደፈለግህ ቦታ፣ጀርመን፣ዩክሬንና ግብጽ ሥራዎች አሉን።

- እምቢ ብልስ?

- ጉዳዩ የመርህ ሳይሆን የጥቅም ወይም የስልጣን ጉዳይ መሆኑ ግልጽ ይሆናል ! ያ ከሆነ ደግሞ ሁሉንም እንደ አመጣጡ አስተናግዳለሁ።

- አስቤበት ነገ መልስ እሰጥሃለሁ።

- መልስ የምትሰጠው ለኔ ነው . . ለሁሉም የሥራ አመራር ቦርድ አባላት አይደለም።

- እሽ ቃሌ ነው . .

ጆርጅ የኩባንውን ግቢ ለቆ ወጣ፤ወደ መኪናው ሲያመራ ለቶም ደወለ . .

- አሁን ብመጣ ይመቸሃል?

- አዎ መምጣት ትችላለህ።

- ከግማሽ ሰዓት በኋላ እደርሳለሁ፣መንገድ ላይ ነኝ።

ጆርጅ ወደ ቶም ክሊኒክ ደርሶ ሲገባ እንግዳ መቀበያው ውስጥ አዲስ ሠራተኛ ገጠመው፣ሠራተኛው እንኳን ደህና መጣህ ብሎ ተቀበለው . .

- ዶክተር ቶም አንተ እየጠበቀ ነው ግባ።

- ጆርጅ እንኳን ደህና መጣህ . . ክሊኒኩ ተመልሶ ከተከፈተ ወዲህ የመጀመሪያው ታካሚ ነህ፣ገና ዛሬ ነው የተከፈተው፤ከነገ ጀምሮ እንጂ ለማንም ደንበኛ ቀጠሮ አልሰጠንም።

- መልካም ዜና ነው፤ይቅርታ ነገሩን ሳልከታተል፣የበራድ ጉዳይ እልባት አገኘ? !

- ላይመለስ ሄዷል።

- ወዴት ሄደ?

- ወደ እስር ቤት፤አደንዛዥ እጽ ሲሸጥ ተይዞ ታሰረ።

- እንዴት እጠላው መሰለህ !

- ለምንድነው የምትጠላው?

- መርህ የሌለው ግለሰብ ነው፤አንድ ሰው መርህ አልባ ሲሆን ከሰው ይልቅ ለዱር አራዊት የቀረበ ይሆናል።

- ፈተናዎች ብርቱ ናቸው ! ከፊቴ ሁለት አማራጮች ነበሩ፤መርሆዬን ረግጬ ሁሉንም ችግሮቼን ወዲያውኑ መፍታት ወይም በመርህ ጸንቼ ወደ ብርቱ ፈተና መግባት። በመርሆዬ ለመጽናት ወስኜ ሁሉንም ነገር ለማጣት ምንም ያህል አልቀረኝም ነበር። በመርህ ላይ መጽናት መጨረሻው ያማረ ስለመሆኑ ግን እርግጠኛ ነበርኩ፣የሆነውም ይኸው ነው።

- የመጣሁበትን ጉዳይ ያወቅህ ትመስላለህ።

- ምንድነው?

ጆርጅ ከካኽ ጋር ስለሆነው ሁሉ ለቶም በዝርዝር ነገረው።
የጉዞውን
ጉዳይም
አንስቶለት ለመሄድ ማቅማማቱን አስረዳው . .

- ላማክርህ ፈልጌ ነው አመጣጤ፣ኢሞራላዊ ቅድመ ግዴታዎቹን ሳልቀበል ጉዞውን ብቀበል መርሆዬን መጣስ ይሆናል ብለህ ታስባለህ?

 

- አልገባኝም፤ለሌላ ሥራ ነው የምትጓዘው እንዴት ነው መርሆህን የምትጥሰው?

- እግረ መንገዴን የካኽን እኩይ ዓላማ አሳካለታለሁ።

- ካኽን ሥራ አመራር ቦርዱ ፊት ይበልጥ ለማጋለጥም ትችል ይሆናል።

- እናም ሀሳብህ እንድጓዝ ነው?

- አዎ . . ወደ ግብጽ ተጓዝ።

- ለምን?

- ቀደም ሲል ባደረግነው ውይይት እስላምን ማጥናት እንዳለብን ተስማምተናል፤አሁን ደግሞ ይህ መልካም አጋጣሚ ተገኝቷል። ክሊኒኩን ዛሬ ባልከፍት ኖሮ እኔ ራሴ ካንተ ጋር በሄድኩ ነበር።

- በቅርቡ ተከታታይ ጉዞዎች በማድረጌ መጓዝ አልወደድኩም፤መጓዝ ካለብኝ ደግሞ ወደ ጀርመን መሄድን ነው የምመርጠው።

- ውሳኔው የራስህ ነው፤እኔ ግን መጓዝህ አስፈላጊ ነው፣ሙስሊሞችን ከውስጥ ሆነህ ታያቸዋለህ፣እንከኖቻቸውንና ስህተቶቻቸውንም የማወቅ እድል ይኖረሃል ባይ ነኝ።

- አስብበታለሁ፤ለማንኛውም አንተ በዚህ ጉዳይ ላይ ያማከርኩት የመጀመሪያው ሰው ነህ። የበለጠ አማክሬና አስቤበት የደረስኩበትን አሳውቀሃለሁ . . ፍቀድልኝ ልሂድ፤ዛሬ በክሊኒክህ ጉዳይ ተጠምደሃል . . በመርህ ላይ መጽናትህ ተገቢህ ነው . . ደህና ሁን።

እየሄደ ለአደም ደውሎ ሊያገኘው እንደሚፈልግ ነገረው። አሁን ዶክተሩ አንዳንድ ምርመራዎችን እያደረገለት በመሆኑ እንደማይመቸው ነግሮት ከይቅርታ ጋር በማታው የሕሙማን መጠየቂያ ሰዓት እጠብቀሃለሁ አለው . . ወደ ቤቱ አመራና የአደምን መጽሐፍ ቅዱስ ቁርኣንን ለማንበብ ወሰነ..
በማንበብ ላይ እያለ ልጆቹ ማይክልና ሳሊ መጡ . .

- ባባ ዛሬ በጊዜ መጣህ !

- አዎ ሥራ ቦታ በጊዜ እንድመጣ የሚያደርገኝ ሁኔታ ስለነበረ ቶሎ መጣሁ።

- ባባ ምንድነው የምታነበው? በተመስጦ ነው ስታነብ የነበረው !

- የሙስሊሞች መጽሐፍ በመባል የሚታወቀውን መጽሐፍ ሳነብ ነበር።

- አሸባሪዎች ተብለው የሚጠሩ ሙስሊሞች?

- አዎ።

- በኛ ትምህርት ቤት የሕንድ ዝርያ ያለው ሙስሊም ተማሪ አለ፤በትምህርት ሰነፍ ሲሆን ጠባዩ በጣም የሚመች ነው፣አሸባሪ ግን አይደለም።

- ሽብርተኝነት ሃይማኖት የለውም፤የሚሉትን አትስማቸው፤ከሰዎች ጋር በመልካም ጸባያቸውና በጥሩ ስነ ምግባራቸው መሰረት ብቻ አብሮነት ይኑርህ።

- ከዐመለ ሸጋነቱ ጋር ግን ከኛ ትንሽ የመገለል ስሜት ይታይበታል።

- ለምን?!

- እኔ እንጃ ! ምናልባት በተደጋጋሚ አሸባሪ ነው ስለሚሉት ወይም አንዳንድ ተማሪዎች በመልኩና በቅርጹ ስለሚያፌዙበት ሊሆን ይችላል።

- ማነው እንደዚያ የሚለው?

- እኔ ግን እንደዚያ ማለት አልወድም። አንዳንድ ተማሪዎች ግን ያደርጋሉ።

- የኔ ልጅ ሰዎችን ከፍ ወይም ዝቅ ሊያደርግ የሚገባው መርሃቸውና ስነ ምግባራቸው ብቻ ነው።

- እቅባልም ልክ እንደዚህ ነው የሚለው።

- እቅባል ማነው?

- የነገርኩህ ሙስሊሙ ሕንዳዊ የትምህርት ቤት ጓደኛዬ ነው።

- አዎ ቁርኣን ውስጥ ፦ {በላጫችሁ በጣም አላህን ፈሪያችሁ ነው፤} (አልሑጁራት፡13) የሚል አንቀጽ ይገኛል። እግዚአብሔርን በመፍራትና ትእዛዛቱን በመፈጸም ደረጃው ካልሆነ በስተቀር ማንም ሰው በቆዳ ቀለሙም ሆነ በዘሩ ምክንያት ከሌላው ሰው አይበልጥም።

- እስላም የዐረቦች ብቻ አይደለም? እቅባል ሙስሊም መሆኑን ሳውቅ በጣም ነው የተገረምኩት !

- የሙስሊሞች ቁጥር አንድ ቢሊዮን በተኩል ያህል ነው፤ከቻይና እስከ አሜሪካ ተሰራጭተው ይገኛሉ። የሚገርመው ደግሞ 80% የሚሆኑ ሙስሊሞች ከዐረቡ ዓለም ውጭ ያሉ መሆናቸው ነው።

- እንዲህ ዓይነቱ እኩልነት እኛም ዘንድም ምነው በኖረ ብዬ ብዙ እመኛለሁ !

- እንዴት ማለትሽ ነው?!

- አንዳንድ ተማሪዎች ከናቴ በወረስኩት የፊቴ ቅርጽና በተክለ ሰውነቴ ምክንያት እንግሊዛዊት አይደለችም፣ሕንዳዊት ናት እያሉ ይንቁኛል።

- የኔ ልጅ ይህ የተከለከለ ነው፣ለአስተማሪሽ ልትነግሪያት ትችያለሽ።

- እነግራታለሁ፤አስተማሪዋ ፊት ብቻ እንጂ መናገራቸውን እንደማያቆሙ ግን አውቃለሁ።

ሕጻናቱ ለቀው ሲወጡ ጆርጅ ከራሱ ጋር አጉረመረመ . .

- ሳሊ እንኳ ሳትቀር በሞራል ሥርዓትና በጥሬ ሞራል መካከል ያለውን ልዩነት ትረዳለች ማለት ነው!

ካትሪና እስከመጣችበት ጊዜ ድረስ ጆርጅ ቁርኣን ማንበቡን ቀጠለበት . .

- ረዥም ቀን ነበር!

- መልካም ፈቃድሽ ከሆነ አንዴ ይቅርታ።

- ምንድነው ምታነበው?

- የሙስሊሞችን መጽሐፍ ነው የማነበው፤የጀመርኩትን እስካጠናቅቅ ጥቂት ትታገሽኝ?

- የት ደርሰሃል?

- ገና አልጨረስኩም።

- በጣም ሰብሰብ ብለህ በጽሞና እያነበብክ ነው ማለት ነው።

- እግዚአብሔር በሙስሊሞች መጽሐፍ ውስጥ የሚለውን አዳምጭማ ፦ {አ.ለ.ረ. (አሊፍ ላም ራ)፤ ይህች (አናቅጽ) ከመጽሐፉ አንቀጾችና ገላጭ ከኾነው ቁርኣን ነው። እነዚያ የካዱት (በትንሣኤ ቀን) ሙስሊሞች በኾኑ ኖሮ ብብዛት ይመኛሉ። ተዋቸው ይብሉ፤ይጠቀሙም፤ተስፋም ያዘናጋቸው በእርግጥም (መጥፎ ፍጻሜያቸውን) ያውቃሉ።} [አልሑጁራት ፡1-3]

- በተለይ ይህን አንቀጽ ወይም ምንባብ ለምን መረጥክ?

- የዚህ መጽሐፍ አንዳንዶቹ ምንባቦች በተለይ ለኔ የተላለፉና እኔን የሚያናግሩኝ ሆነው ለምን እንደሚሰሙኝ እኔ እንጃ፤ከነዚህም ይኸኛው አንዱ ነው።

- በዚህ ምንባብ አንተን የሚያናግረው ምኑ ነው?!

- ገላጭ የኾነው መጽሐፍ . . የካዱ ሰዎች ሙስሊሞች በኾን ኖሮ ብለው አጥብቀው መመኘታቸው . . ከሃዲዎቹን መብላት መጠጣትና መደሰት ያዘናጋቸው መሆኑ . . ይህ ሁሉ እኔን በተለይ የሚያነጋግረኝ ሆኖ ለምን እንደሚሰማኝ አላውቅም?

- ሙስሊም ብሆን ኖሮ ብለህ ትቆጫለህ ማለት ነው?!

- አየሽ ይህ የማይሆን ነው . . ግና ለጥያቄዎቼ መልስ ማግኘት እፈልጋለሁ፤የመታደልን መንገድ ማወቅ እሻለሁ፤ከዚህ ሁሉ በመብላት በመጠጣትና በመዝናናት እንዳልዘናጋ እሰጋለሁ፤ለዚህ ነው አንዳንዶቹ አንቀጾች እኔን በግል የሚመለከቱኝ ሆነው የሚታዩኝ።

- የመታደል መንገድ እስላም ራሱ መሆን አይችልም?!

- እህህ፣ልክ የአደምን አነጋገር አመጣሽ፤ያ ይሆናል ብዬ ባልገምትም በሌሎች ሃይማኖቶች ላይ እንዳደረግሁት ሁሉ ለእስላምም በግምት ላይ የተመሰረተ ሳይሆን በዕውቀት ላይ የተመሰረተ ሳይንሳዊ ምላሽ እሰጣለሁ።

- በነገራችን ላይ አደም እንዴት ሆኖ ይሆን?

- አንቺ ነሽ ከኔ በኋላ ያየሽው፣በሥራ ቦታ ብዙ ጉዳዮች ስለ ተፈራረቁብኝ ዛሬ አልጠየቅሁትም።

- የምስራች በለና፣ምን አዲስ ነገር ተገኘ?!

- መርሆዬን ሳልጥስ ወደ ጀርመን እንድጓዝ ካኽ አዲስ ሀሳብ አቅርቦልኛል።

- ተቀብለህ ችግሩ እልባት አግኝቷል ማለት ነው?

- አይደለም፣አስብበታለሁ ነው ያልኩት፤በዚህ ወቅት መሄድ ግን አልፈልግም።

- እናም አሁን ጉዳዩ የሀሳብ ልዩነት እንጅ ምንም ያህል የመርህ ችግር አይደለም ማለት ነዋ?

- ካኽም እንደዚህ ነው ያለኝ . . እውነቱን ለመናገር ግን ከዚያ በኋላ ሌላ ምክንያት ተፈጥሮ ነው፤ቶምን አማክሬ ስለነበር ሌላ ሀሳብ አቀረበ።

- የቶም ሀሳብ ምንድነው?!

- ወደ ግብጽ እንድጓዝ ነው የሚፈልገው።

- ጀርመን አላልከኝም ነበር?

- ካኽ ወደ ጀርመንን፣ግብጽ ወይም ዩክሬን የመጓዝ ሦስት አማራጮችን የሰጠኝ ሲሆን ቶም ግን ወደ ግብጽ እንድጓዝ እየጎተጎተኝ ነው።

- እናም ለጥያቄዎችህ ምላሽ ፍለጋ ነው ማለት ነው?

- አዎ፣እንደ ጀርመን ያለውን የሰለጠነ ጠንካራ አገር ትቼ ወደ ኋላ ቀር የአፍሪካ አገር መሄድ ግን አልፈልግም።

- ግብጽ እስላምና ሙስሊሞችን ከማወቅ ባሻገር የኮፕት ክርስቲያኖች፣የናይልና የፒራሚዶች አገርም ነች።

- ግብጽን በሚገባ የምታውቂ ትመስያለሽ!

- አዎና፣የቅብጥ ኦርቶዶክስ ክርስትና አገር፣ከዓለም አስደናቂ ነገሮች አንዱ የሆኑት የፒራሚዶች አገር፣በዓለም ረዥሙ ወንዝ ናይል የሚፈስባት አገር . . ናት። ዘውትር ካቶሊካዊነቴን ከሚተች አንድ ኮፕቲክ ኦርቶዶክስ ጋር ትውውቅ አለኝ . . እኛ እናንት ፕሮቴስታንቶችን በለዘብተኝነትና በግድ የለሽነት እንደምንወቅሰው እርሱ ደግሞ ካቶሊኮችን በሃይማኖታዊ ጉዳዮች ላይ ግድ የለሾች መሆናቸውን ይተቻል።

- እኛ ከእናንተ እንደተገነጠልን እናንተም በተራችሁ ከነሱ የተገነጠላችሁ ስለሆነ ነዋ! እናም አንቺም እንደ ቶም ሁሉ ከጀርመን ይልቅ ወደ ግብጽ መሄዴን ትደግፊያለሽ ማለት ነው?

- ሊሆን ይችላል፣ለማንኛውም ግን ውሳኔው ያንተ ነው። እኔ የጥንታዊ ስልጣኔ ባለቤት የሆኑ አገሮችን እወዳለሁ፣አንተ ደግሞ ምናልባት በዘመናዊ ስልጣኔ የተራመዱ አገሮችን ትወድ ይሆናል። በሕንድ ጉዞህ ግን ደስተኛ ነበርክ።

- በነገሩ ላይ አስብበታለሁ፤አንቺ ግን በመርህ ደረጃ ጉዞውን የደገፍሽ ትመስያለሽ።

- ከተከታታይ ጉዞዎችህ በኋላ ከኛ ጋር ቆይተህ ማረፍህን ብፈልግም፣መርሆውን መጣስ ለአንድ ሰው ራሱን ከማጣት የተለየ አይደለም። በመርሆህ የሙጥኝ ብለህ መጽናት ምናልባት ሥራህን የማጣት ዋጋ ሊያስከፍልህ ይችል ይሆናል፤እናም ይኸኛው ላንተ ጥሩ መውጫ መንገድ ነው።

- አዎ፣ይህ የተሻለ አማራጭ ሳይሆን አይቀርም፤ለማንኛውም እስከ ነገ ድረስ ጊዜ ስላለኝ አስብበታለሁ። ያንቺን በተመለከተስ አዲስ ነገር አለ?

- አዎ፣የኔም እልባት ሳያገኝ የቀረ አይመስለኝም።

- እልባት?! በምን ተደመደመ?

- የያዝነው ወር እነሱ ዘንድ የምሠራበት የመጨረሻው ወር ይሆናል ብዬ አስባለሁ።

- ከዚያስ?

- ሌላ ቦታ ለሥራ አመልክቼ በሂደት ላይ ነኝ፤የደረስኩበትን በተከታታይ ስለማሳውቅህ ምንም ልታስብ አይገባም። አሁን ለሳሊና ለማይክል ምሳ ላዘጋጅ።

ለውጥና ሽግግር (4)

በማታው የሕሙማን መጠየቂያ ሰዓት ጆርጅ አደምን ለመጠየቅ ወደ ሆስፒታሉ አመራ . . ወደ ክፍሉ ሲገባ ከሸይኽ ባስም ጋር እየተጨዋወቱ ሲስቁ አገኛቸው . .

- እንደምን ዋላችሁ፣ዛሬ ሁለታችሁም ደስተኞች ትመስላላችሁ።

- አልሐምዱሊላህ እኔ ሁሌም ደስተኛ ነኝ፣ከወንድሜ ከአደም ጋር በመሆኔ ደስታዬ ዛሬ ከወትሮው የበለጠ ሆኗል፤አንተስ እንዴት ነህ?

- ደህና ነኝ፤አደም እንዴት ነህ አሁን?

- እግዚአብሔር የተመሰገነ ይሁን በጥሩ ሁኔታ ላይ ነኘ።

- አመጣጤ አንተን ለማየትና በሆነ ጉዳይ ላይ ላማክርህ ነበር !

- ደስ ይለኛል፣ቀጥል።

- ብዙ ሳላራዝምብህ ከመርሆዬና ከሥራዬ አንምዱን የመምረጥ ፈተና ውስጥ ገብቼ ከብዙ ትግል በኋላ መርሆዬን መርጫለሁ፤ነገሮች የተስተካከሉ ቢሆንም ካልተጠበቀ ድንገተኛ የጉዞ ግዴታ ጋር ነው።

- በመርሁ ላይ የሚጸና ማንኛውም ሰው ውድቀት የሚያጋጥመው መስሎ ቢታየው እንኳ በመጨረሻ ድል አድራጊ ይሆናል።

ባስም ፈገግ ብሎ

- እኔም አንዳክልበት ፍቀዱልኝ፣ቁርኣን ውስጥ ነብያት በመርህ ላይ በመጽናታቸውና በትዕግስታቸው እንዴት ድል አድራጊዎች እንደሆኑ አላነበብክም?

- ቁርኣን ውስጥ እንደተመለከተው ሁሉ እናንተ ሙስሊሞች ዘንድ ሁሉም ነብዮች ድል አድራጊዎች ናቸው። እናንተ ዘንድ ዒሳ እንኳ ሳይቀር ድል አደረገ እንጂ አልተገደለም፤በእኛ ዘንድ ያለው ግን ኢየሱስ የሰው ልጆችን ለማዳን ነፍሱን ሰውቶ ተገደለ የሚል ነው።

ባስም በፈገግታ፦

- እህህ፣ስለዚህም እስላም ለዒሳ (ሰላም በርሳቸው ላይ ይሁን) የተለየ አክብሮት አለው፣ከናንተ ይበልጥ ይወዳቸዋል።

- ይሁን እንጂ ከሰብአዊ ፍጡርነት የወጣ ልዩ ባህሪ እንዳለውም ሆነ ለሰው ልጅ ቤዛ መሆኑን ግን አይቀበልም።

- እንዳውም ከዚያ የተሻለ አክብሮትና ልቅና ይሰጣቸዋል፤ቁርኣንን ያነበብክ አትመስልም፤የነብዩ ዒሳን (ሰላም በርሳቸው ላይ ይሁን) ታሪክ ቁርኣን ውስጥ ብዙ ቦታ ላይ አላነበብክም?

- ትርጉሙን ካንተ የወሰድኩት ገና ትናንት ነው፤ይሁን እንጂ አብዛኛውን አንብቤአለሁ፣የኢየሱስንም ታሪክ አንብቤአለሁ።

- አብዛኛውን ካነበብክ ዘንዳ በመርየም ምዕራፍ ውስጥ በዒሳ አንደበት የተነገረውን የአላህ ቃል ትርጉም አንብበሃል ብዬ አስባለሁ ፦ {በየትም ስፍራ ብሩክ አድርጎኛል፤በሕይወትም እስከ አለሁ ሶላትን በመስገድ ዘካንም በመስጠት አዞኛል።} [መርየም፡21] {ሰላምም በኔ ላይ ነው፣በተወለድሁ ቀን በምሞትበትም ቀን፣ሕያው ኾኘ በምቀሰቀስበትም ቀን፤} [መርየም፡33] በኣሊ ዒምራን ምዕራፍም እንዲህ ይላል ፦ {ወደ እስራኤልም ልጆች መልክተኛ ያደርገዋል፤(ይላልም) ፦ እኔ ከጌታዬ ዘንድ በታምር መጣኋችሁ። እኔ ለናንተ ከጭቃ እንደ ወፍ ቅርጽ እፈጥራለሁ፤በርሱም እተነፍስበታለሁ፤በአላህም ፈቃድ ወፍ ይኾናል። በአላህም ፈቃድ ዕውር ኾኖ የተወለደን፣ለምጸኛንም አድናለሁ፤ሙታንንም አስነሳለሁ። የምትበሉትንና የምታደልቡትንም ሁሉ እነግራችኋለሁ፤የምታምኑ እንደ ኾናችሁ ለእናንተ በዚህ ውስጥ ታምር አለበት።} [ኣሊ ዒምራን፡49]

- አዎ የጠቀስካቸውን ሁሉ አንብቤአለሁ፤በጣም የሚደንቀው ግን ለክርስትና ያላችሁ አክብሮት ነው !

- ግልጽነትን ትወዳለህ?

- እህህ፣በእርግጠኝነት አዎ።

- እናንተ የኛን ያህል ለዒሳ (ሰላም በርሳቸው ላይ ይሁን) ተገቢውን ክብር አትሰጡም።

- እንዴት?

- እናንተ ተስቅለዋል ብላችሁ ታምናላችሁ፣እኛ ግን አላህ ከጠላቶቻቸው ተንኮል አድኗቸው ከፍ አደረጋቸው እንጂ አልተገደሉም ብለን ነው የምናምነው። የሚከተለውን የአላህ ቃል አላነበብክም ፦ { . . አልገደሉትም፤አልሰቀሉትምም፤ግን ለነሱ (የተገደለ ሰው በዒሳ) ተመሰለ፤ . . } [አል ኒሳእ፡157]

- ልክ ነው፣አንብቤአለሁ።

- እናንተ ወይም ቢያንስ አንዳዶቻችሁ ንጽህቱ መርየም (ሰላም በርሳቸው ላይ ይሁን) አላህ ከእንዲህ ዓይነቱ አነጋገር ይጠብቀንና ዝሙት ፈጽማለች ብላችሁ ታምናላችሁ።

- እናንተስ የኢየሱስ አባት ማነው ብላችሁ ነው የምታምኑት?

- አባት የለውም፣አላህ አደምን ካለ አባትና ካለ እናት እንደ ፈጠረ ሁሉ ዒሳን ካለ አባት ከእናቱ ፈጥሮታል፤ለዚህ ነው ገና ጨቅላ ሕጻን ሆኖ የእናቱን ንጽሕና ለማረጋገጥ አላህ እንዲናገር ያደረገው።

- ከሰው ልጆች አባት ከአደም (ሰላም በርሳቸው ላይ ይሁን) ጀምሮ ላሉት መለኮታዊ ሃይማኖቶች ሁሉ የላቀ አክብሮት አለን፤ሁሉም ነብያት ጥሪ ያደርጉ የነበረው ለአንድ መሰረታዊ ጉዳይ ሲሆን እሱም ተውሒድ ወይም የአላህን አንድና ብቻ እውነተኛ አምላክነት ማረጋገጥ ነው። እያንዳንዱ ነብይም ከርሱ ቀጥሎ ለሚመጣው ነብይ መንገድ በማመቻቸት መምጣቱን ያበስር ነበር። በትርጉሙ ውስጥ የሚከተለውን አላነበብክም ፦ {የመርየም ልጅ ዒሳ ፦ የእስራኤል ልጆች ሆይ እኔ ከተውራት በፊት ያለውን የማረጋግጥና ከኔ በኋላ በሚመጣው መልክተኛ ስሙ አሕመድ የማበስር ስኾን፣ወደናንተ (የተላክሁ) የአላህ መልክተኛ ነኝ ባለ ጊዜ (አስታውስ)፤በግልጽ ታምራቶች በመጣቸውም ጊዜ ይህ ግልጽ ድግምት ነው አሉ።} [አል ሶፍ፡6] በናንተ መጽሐፍ ውስጥም ይህንኑ የሚያረጋግጥ አለ አይደለም?!

 

- የለም፣ያልከውን ነገር አላነበብኩም፤ምናልባት ገና ባላነበብኩት ቀሪ ክፍል ውስጥ ይኖር ይሆናል። እኛ ዘንድም በአንዳንዶቹ መጽሐፎቻችን ውስጥ ብቻ ያልከው ነገር ሰፍሯል።

- የወንጌል ችግር ከኦሪጂናሉ መዛባቱ፣መከለሱና መለዋወጡ፣በተለያየ አጻጻፍ በተለይም ክርስቲያኖች በአይሁዶች እጅ ስቃይና መከራ ይደርስባቸው በነበረበት ዘመን በተደጋጋሚ መጻፉ ነው።

- ይህ የሁሉም መለኮታዊ መጽሐፎች ችግር ይመስለኛል፣ያልተዛባ፣ያልተከለሰና ሳይለወጥና ሳይምታታ ኦሪጂናል ቅጂውን እንደ ጠበቀ የሚገኝ አንድ መጽሐፍ እንኳ እስኪ አምጣልኝ።

- ቁርኣን ፈጽሞ አልተዛባም፣በጭራሽ አልተለዋወጠም፤ይህ በሙስሊሞች ዘንድም ሆነ ሙስሊም ባልሆኑትም ዘንድ የተረጋገጠ ነው። ይህ ብቻ ሳይሆን በሰው ልጆች ታሪክ ውስጥ ከቁርኣን ይበልጥ ጥንታዊነቱን ባለበት ጠብቆ ሳይጨምር፣ሳይቀንስና ሳይበረዝ በትክክል የተላለፈ ሌላ ሰነድ የለም፤ይህም ሙስሊም ባልሆኑ ወገኖች ዘንድም ተቀባይነት ያለው ይመስለኛል። ከነብዩ ብዙ ሺ ሰዎች ናቸው ሰምተው ያስተላፉት፣እነሱም በተራቸው ለብዙ ሺ ሰዎች አስተላልፈዋል፤በዚህ ሂደት ውስጥ ያንዲት ፊደል ወይም ከዚያ ያነሰ ልዩነት እንኳ አልተፈጠረም።

- ከፊደል ያነሰ ምንድነው? !

- ቁርኣን የራሱ የሆነ የአነባበብ ስልትና የድምጽ አወጣጥ አለው። ይህ እንኳ ሳይቀር ሲወርድ ሲዋረድ የመጣና በነበረበት ሁኔታ ተጠብቆ የኖረ ነው።

- በተለያዩ ቅጂዎቹ መካከል ምንም ልዩነት አይታይም ?

- ፈጽሞ የለም፣እርግጥ ነው ሲወርድ ሲዋረድ የመጡ የተለያዩ የአነባበብ ስልቶች (ቅራኣት) ይገኛሉ፣ከዚህ ውጭ ሌላ ልዩነት የለም።

- ከአነጋገርህ እንደምረዳው ለምሳሌ ኢየሱስ በአንዱ የአነባበብ ስልት ተገድሏል፣በሌላው አነባበብ ደግሞ ራሱን አድኗል የሚል ሊሆን ይችላል?

- አይችልም ! ቁርኣን አንድና አንድ ብቻ ነው፣ምንም ልዩነት የለበትም። ያልኩት የአነባበብ ዘዬ ልዩነት ብቻ ነው፤የንባብ ዘዬ ልዩነቱ በአብዛኛው ትርጉሙንም ሆነ ቃላቱንም እንኳ የማይነካ የድምጼ አወጣጥ ልዩነት ብቻ ነው።

- እስከዚህ ደረጃ ድረስ? ! ትንሽ ያጋነንክ መሰለኝ!

- የናንተ አውራፓውያን ተመራማሪ ሊቃውንት የሚሉትን ብታነብ ልክ አሁን ከምነግርህ ጋር ቃል በቃል የተጣጣመ መሆኑን መረዳት ትችላለህ።

- ግና . . ከሚገባው በላይ ያጋነንክ ወይም ትንሽ ስሜታዊ የሆንክ አይመስልህም?

- ምናልባት ሊሆን ይችላል አንተ ግን ከረዥም ጊዜ ጀምሮ ለጥያቄዎችህ ምላሽ ለማግኘት ፍለጋ ላይ መሆንህን አደም ነግሮኛል። ሁሉንም ሃይማኖቶች ተራ በተራ የመረመርክ መሆንህንና እስላምን በማወቅና በመመርመር ሂደት ላይ እንደምትገኝ፣በእውነታ ላይ የተመሰረተ ሚዘናዊ ሳይንሳዊ አቀራረብ እንደምትወድም ነግሮኛል።

አደም ጣልቃ ለመግባት ተመቻችቶ ተቀመጠ፦

- ድንቅ ውይይት ነው፤በማቋረጤ ግን ይቅርታ ይደረግልኝ . . ጆርጅ ልታማክረኝ የነበረው በምን ጉዳይ ላይ እንደሆነ ንገረኝ።

- ባስም የመጣሁበትን ጉዳይ አስረሳኝ።

- ጆርጅ ይቅርታ አድርግልኝ።

- ዋነው ነገር . . በመርሆዬ ከጸናሁ በኋላ ወደ መስቀለኛ መንገድ ደረስኩ፤ከመርሆዬ ጋር የማይጻረር የሥራ ጉዞ ማድረግ ወይም ሥራዬን መልቀቅ እንደ አማራጭ ቀርቦልኛል። ሀሳቤ ወደ መጓዙ ያጋደለ ቢሆንም አንዳንዴ ጉዞ የሰለቸኝ ሆኖ ይሰማኛል።

- ካንዱ ጉዞ ሳታርፍ ሌላ ጉዞ !

- ልክ ነህ፣እውነቱን ለመናገር በአሁኑ ወቅት የመጓዝ ፍላጎት የለኝም፤በሥራ መስክ ለገጠመኝ ቀውስ ግን ተመራጩ መፍትሔ ይመስለኛል።

- የአካል ድካም የራስን መርሆ ከመጣስ ይቀላል፤አንድ ሰው የራሱን መርሆ ከጣሰ ግን አካሉ ብቻ ሳይሆን ነፍሱም ትደክማለች። ለመሆኑ ጉዞው ወዴት አገር ነው?

- ወደ ጀርመን፣ወደ ዩክሬን ወይም ወደ ሌላ አገር ነው።

- ወደ አንዱ እስላም አገር ቢሆን ምኞቴ ነበር፤ምድራዊ ሰው ሰራሽ ሃይማኖቶችን ለማወቅና ለመመርመር፣በመቀጠልም መለኮታዊ ሃይማኖቶችን - አይሁዳዊነትንና ክርስትናን - ለማወቅና ለመመርመር እንደ እንደ ተጓዝክ ሁሉ እስላምን በይበልጥ ለማወቅና በቅርበት ለመረዳት ጉዞ እንድታደርግ ስመኝ ነበር።

- ጀርመን፣ዩክሬን ወይም ግብጽ።

- አደም መሬት መሬቱን እያየ እጆቹን ለቀቅ አደርጎ ፦ ወይኔ ግብጽ እንዴት እንደናፈቀችኝ ልነግራችሁ አልችልም፤እኔና ሸይኽ ባስም ከግብጽ ነን፤ወደ ግብጽ ከተጓዝክ እስላምን በይበልጥ ማወቅ ትችላለህ ብዬ አስባለሁ።

- አንተ ግብጻዊ ነህ? !

- አዎ . . ከዚህ በፊት የነገርኩህ ይመስለኛል።

- ሊሆን ይችላል፣አላስታውስም።

- ወደ ግብጽ ከሄድክ ወዳጆቼ እዚያ አቀባበል እንዲያደርጉልህ እነግራቸዋለሁ፤አገሩን ያሳዩሃል፣ወደ ቱሪስት መዳረሻዎች ይወስዱሃል።

ባስም ደስታ በተሞላው ቅላጼ፦

- ወንድሜ ካይሮ ውስጥ የፊዚክስ መምህር ነው፣የምትፈልገውን ሁሉ ሊያመቻችልህ ይችላል።

- ፍላጎቴ ወደ ጀርመን መሄድ ቢሆንም ያማከርኳቸው ሁሉ ወደ ግብጽ ሂድ እያሉኝ መሆኑ ነው የሚገባኝ፤ምናልባት ነገ ለካኽ ወደ ግብጽ እንደምሄድ አሳውቀው ይሆናል።

- እኔም ለወንድሜ ለመንገር ያንተን ምላሽ እጠብቃለሁ።

- ካንተ ጋር መጓዝ ብችል ኖሮ ግብጽ ናፈቃኛለች። ሰዎቹ፣አገሩና ሁሉም ነገሯ ናፍቆኛል፤ከመጣሁ ሁለት ዓመት ያህል ሆነኝ።

- ታዲያ ከኔ ጋር ለምን አትጓዝም?

- በአላህ ፈቃድ ተነገ ወዲያ ከሆስፒታል እወጣለሁ፤የዩኒቨርሰቲ ፈተና ከሦስት ሳምንት በኋላ ነው።

- ደህና መሆንህ በራሱ በቂ ነው፤አንተና ባስም ከግብጽ እንዳመጣላችሁ የምትፈለጉት ስጦታ ምንድነው?

- እህህ፣ ራሷን ግብጽን እንዳለች አምጣልኝ።

- እህህ።

ማታ ላይ ጆርጅ ኢሜይሉን ከፈተ፤ቁርኣንን አስመልክቶ ልኮላቸው ለነበረው መልክት ከወዳጆቹ የተላኩለት ምላሾች በተከታታይ ደርሰዋል። ሁሉንም አንድ ላይ ጨምቆ ማጠቃለያውን ለሁሉም መልሶ ላከላቸው . .

‹‹ሌቪ ግልጽ መልስ የለኝም፤ከፊሉን ብቻ ነው ያነበብኩት፤ጊዜው በቂ አልነበረም።

ሐቢብበአስተላለፉ ከተቀሩት መለኮታዊ መጽሐፍት ሁሉ የበለጠ ተአማኒነት ያለው ነው።

ቶም ይቅርታ . . በክሊኒኩ ጉዳይ ተወጥሬ ነበር፤ከሙስሊሞች መጽሐፍ ቅዱስ በጣም ጥቂቱን ብቻ እንጂ አላነበብኩም፣ግን አነበዋለሁ።

ካትሪናበእርግጥ ከእግዚአብሔር ዘንድ የተላለፈ ይመስለኛል።

ጃኖልካቁርኣን ያለ ምንም መዛባት ከሙሐመድ የተላለፈ መሆኑ በሳይንሳዊ መንገድ የተረጋገጠ ነው። በሙሐመድ የሚያምን ሰው ቁርኣን ከእግዚአብሔር ዘንድ የተላለፈ መሆኑን አምኖ መቀበል ይኖርበታል።››

ዱብ ዕዳ የሆነበት ነገር ጃኖልካ በመልክቱ መጨረሻ ስሙን ካሰፈረ በኋላ ትሪፖሊ - ሊብያ ብሎ ማስከተሉ ነበር። ከዚያም ለአዲስ ደብዳቤ ዊንዶ ከፈተ . . ለሁሉም የሚከተለውን ጻፈላቸው . .

‹‹ስምንተኛው መልክትእስላምን በይበልጥ እንድናውቅ እፈልጋለሁ፤ለአስቸኳይ ጉዳይ ወደ ግብጽ አገር ሳልሄድ አልቀርም። በመሆኑም

1. እስላምን ወይም ግብጽን ለማወቅ ዋቢ መጻሕፍትና መጣቀሻዎችን የሚጠቁመኝ ሰው ካለ፤

2. ለውይይት የሚቀርቡ ወይ ሊነሱ የሚገቡ ጥያቄዎች ያሉት ሰው ቢኖር፤

3. ማድረስ የሚገቡ መልሶች ያሉት ሰው ቢኖር፤

መልሶቻችሁን በሁለት ወይም ሦስት ቀናት ውስጥ እጠብቃለሁ። እንደ ተለመደው ጨምቄ ማጠቃለያውን መልሼ እልክላችኋለሁ።

ጆርጅ››