የነቢይነት አስረጅ ምልክቶች

የነቢይነት አስረጅ ምልክቶች

አላህ (ሱ.ወ.) ወደ ባሮቹ የላካቸው ነቢያትና መልክተኞች፣ጥሪያቸውና ትምሕርታቸው እውነተኛ ስለመሆኑ፣በእርግጥ ከርሱ የተላኩ ስለመሆናቸው አስረጅና ማረጋገጫዎችን አላህ ሰጥቷቸዋል። ይህም በነርሱ ላለማመንና እነርሱን ላለመታዘዝ በሰዎች ዘንድ ምንም ማመካኛ እንዳይኖር ለማድረግ ነው። አላህ (ሱ.ወ.) እንዲህ ብሏል፦

{መልክተኞቻችንን በግልጽ ማስረጃዎች በእርግጥ ላክን፤}[አል ሐዲድ፡25]

የመልክተኞቹን እውነተኛነት የሚያረጋግጡ እነዚያ ማስረጃዎች ብዛት ያላቸው ሲሆኑ፣ከዋነኞቹ ውስጥ የሚከተሉትን እናገኛለን፦

1- አላህ (ሱ.ወ.) መልክተኞችንና ነቢያትን በምልክቶችና በተአምራት ያግዛቸዋል።

እነዚህም ሰዎች ሊያደርጓቸው የማይችሉ ከተለመዱ የተፈጥሮ ሕግጋት ውጭ የሆኑና በመልክተኞቹና በነቢያቱ እጅ የሚፈጸሙ ትንግርታዊ ነገሮችና ክስተቶች ናቸው። ከነዚህ መካከል ወደ እባብነት የሚለወጠው የሙሳ [የአላህ ሰላም በርሳቸው ላይ ይሁን] በትር አንዱ ነው። አላህ (ሱ.ወ.) እንዲህ ብሏል፦

{ሙሳ ሆይ! ይህችም በቀኝ እጅህ ያለችው ምንድን ናት? (ተባለ)። ፦ እርሷ በትሬ ናት፤በርሷ ላይ እደገፍባታለሁ፤በርሷም ለፍየሎቼ ቅጠልን አራግፍባታለሁ፤ለኔም በርሷ ሌሎች ጉዳዮች አሉኝ፣አለ። (አላህም) ሙሳ ሆይ! ጣላት አለው። ጣላትም፤ወዲያውኑ እርሷ የምትሮጥ እባብ ኾነች። ፦ ያዛት፤አትፍራም፤ወደ መጀመሪያ ጠባይዋ እንመልሳታለን አለው። እጅህንም ወደ ብብትህ አግባ፤ሌላ ታምር ስትኾን ያለ ነውር ነጭ ኾና ትወጣለችና። ከታምራቶቻችን ታላቋን እናሳይህ ዘንድ፣(ይህን ሠራን)።}[ጣሃ፡17-23]

የነብዩ ዒሳ [የአላህ ሰላም በርሳቸው ላይ ይሁን] ተአምር ደግሞ በአላህ ፈቃድ ዲዳ ሆኖ የተወለደን ሰውና ለምጻምን መፈወስ ነበር። ድንግል ማርያም በዒሳ ልደት [የአላህ ሰላም በሁለቱም ላይ ይሁን] በተበሰረች ጊዜ በርሷ አንደበት አላህ (ሱ.ወ.) እንዲህ ብሏል፦

{፦ ጌታዬ ሆይ! ሰው ያልነካኝ ስኾን፣ለኔ እንዴት ልጅ ይኖረኛል? አለች፤ነገሩ እንደዚህሽ ነው፤አላህ የሚሻውን ይፈጥራል፤አንዳችን በሻ ጊዜ፣ለርሱ ኹን ይለዋል፤ወዲያውኑም ይኾናል፣አላት። ጽሕፈትንና ጥበብንም፣ተውራትንና ኢንጂልንም ያስተምረዋል። ወደ እሥራኤልም ልጆች መልክተኛ ያደርገዋል፤(ይላልም)፦ እኔ ከጌታዬ ዘንድ በታምር መጣኋችሁ። እኔ ለናንተ ከጭቃ እንደ ወፍ ቅርጽ እፈጥራለሁ፤በርሱም እተነፍስበታለሁ፤በአላህም ፈቃድ ወፍ ይኾናል። በአላህም ፈቃድ ዕውር ኾኖ የተወለደን፣ለምጸኛንም፣አድናለሁ፤ሙታንንም አስነሳለሁ። የምትበሉትንና በቤታችሁ የምታደልቡትንም ሁሉ እነግራችኋለሁ፤የምታምኑ እንደኾናችሁ ለእናንተ በዚህ ውስጥ በእርግጥ ታምር አለበት። ከተውራትም ከኔ በፊት ያልለውን ያረጋገጥሁ ስኾን፣የዚያንም በናንተ ላይ እርም የተደረገውን ከፊል ለናንተ እፈቅድ ዘንድ፣(መጣኋችሁ) ከጌታችሁም በኾነ ታምር መጣኋችሁ። አላህንም ፍሩ፤ታዘዙኝም። አላህ ጌታየና ጌታችሁ ነው፤ስለዚህ ተገዙት፤ይህ ቀጥተኛ መንገድ ነው (አላቸው)።}[ኣሊ ዒምራን፡47-51]

የነብዩ ሙሐመድ [የአላህ ሰላምና እዝነቱ በርሳቸው ላይ ይሁን]፣ታላቁ ተአምር የማያነቡና የማይጽፉ ነቢይ ከመሆናቸውም ጋር ታላቁ ቁርኣን ነው። አላህ (ሱ.ወ.) እንዲህ ብሏል፦

{፦ ሰዎችም ጋኔኖችም የዚህን ቁርኣን ብጤ በማምጣት ላይ ቢሰባሰቡ፣ከፊላቸው ለከፊሉ ረዳት ቢኾንም እንኳ፣ብጤውን አያመጡም፤በላቸው። በዚህም ቁርኣን ውስጥ ከምሳሌው ሁሉ ለሰዎች በእርግጥ መላለስን፤አብዛኞቹም ሰዎች፣ክሕደትን እንጂ ሌላን እምቢ አሉ።}[አል እስራእ፡88-89]

የመልክተኞችና የነቢያት ታምራት እነዚህና ሌሎችም ነበሩ።

አላህ (ሱ.ወ.) ለመልክተኞችና ለነብዮች የሰጣቸውን ምልክቶችና ታምራት ስናስተነትን በሦስት ጉዳዮች ስር የሚካተቱ ሆነው እናገኛቸዋለን። እነሱም፦ ዕውቀት፣ችሎታና መብቃቃት ናቸው። ከሕዋሳዊ ግንዛቤ ውጭ የሆኑ ያለፉና የሚመጡ ጉዳዮችን በተመለከተ፣ነቢዩ ዒሳ ለሕዝባቸው የሚበሉትንና በየቤቶቻቸው የሚያስቀምጡትን መንገራቸው፣ነብያችን ሙሐመድም ስላለፉት ሕዝቦች፣ወደፊት ስለሚከሰቱ ተፈታታኝ ሁኔታዎችና ለትንሣኤ ቀን መምጫ መቃረብ ምልክት ስለሆኑ ምልክቶች የተናገሯቸው ትንቢቶች፣ . . እነዚህ ሁሉ በዕውቀት ስር የሚካተቱ ናቸው። የበትር ወደ እባብነት መለወጥ፣ዲዳንና ለምጻምን መፈወስ፣ሙታንን ማስነሳት፣አላህ መልክተኛው ሙሐመድን  ከሰዎች ጥቃት መጠበቁ፣እነዚህ ደግሞ በችሎታ ስር የሚካተቱ ታምራት ናቸው። አላህ (ሱ.ወ.) እንዲህ ብሏል፦

{አንተ መልክተኛ ሆይ! ከጌታህ ወደ አንተ የተወረደውን አድርስ፤ባትሠራም (ጥቂትንም ብታስቀር) መልክቱን አላደረስክም፤(አድርስ) አላህም ከሰዎች ይጠብቅሃል፤አላህ ከሓዲዎችን ሕዝቦች አያቀናምና።}[አል ማእዳህ፡67]

እነዚህ ታምራቶች የሚሞረኮዙባቸው ሦስቱ ነገሮች ማለትም ዕውቀት ችሎታና መብቃቃት፣በተሟላና ፍጹማዊ በሆነ መልካቸው ለአላህ ብቻ የተገቡ ናቸው። (3)

2- ቀዳሚዎቹ ነብያት በቀጣይ ስለሚመጡ ነቢያት ማብሰራቸው፦

ከነብይነት ማረጋገጫዎች አንዱ፣የቀደሙ ነቢያት ከነሱ በኋላ ስለሚመጡ ነቢያት ለሕዝቦቻቸው ብስራት መንገራቸው ነው። እያንዳንዱ ነብዩ ሙሐመድ  በርሱ የሕይወት ዘመን ከአላህ ከተላኩ አምኖ ሊከተላቸው አላህ (ሱ.ወ.) ቃል ኪዳን አስገብቶታል። አላህ (ሱ.ወ.) እንዲህ ብሏል፦

{አላህ የነቢያትን ቃል ኪዳን፣ከመጽሐፍና ከጥበብ ሰጥቻችሁ ከዚያም ከእናንተ ጋር ላላው (መጽሐፍ) የሚያረጋግጥ መልክተኛ ቢመጣላችሁ፣በርሱ በእርግጥ እንደምታምኑበት በእርግጥም እንድትረዱት ሲል በያዘ ጊዜ (አስታውስ)፤አረጋገጣችሁን? በይሃችሁ ላይ ኪዳኔን ያዛችሁም? አላቸው፤አረጋገጥን አሉ፤እንግዲያስ መስክሩ፤እኔም ከእናንተ ጋር ከመስካሪዎቹ ነኝ አላቸው።}[ኣሊ ዒምራን፡81]

3- የነቢያትን ሁኔታ መመልከት፦

ነብዮችና መልክተኞች ከሕዝቦቻቸው ጋር ተቀላቅለው በአብሮነት ይኖሩ ነበር። ከዚህም ሰዎች ስለ ማንነታቸውና ስለ ስነምግባራቸው በቀላሉ ይረዳሉ፤በሚያስተምሩት ነገርም እውነተኞች መሆናቸውን ይገነዘባሉ። አይሁድ ንጹይቱን መርየምና የአላህን ነብይ ዒሳን [የአላህ ሰላም በሁለቱም ላይ ይሁን] በወነጀሉ ጊዜ፣አላህ (ሱ.ወ.) የሁለቱን እውነተኛነት ግልጽ አድርጓል። አላህ (ሱ.ወ.) እንዲህ ብሏል፦

{በርሱም የተሸከመችው ኾና ወደ ዘመዶቿ መጣች፤- መርየም ሆይ! ከባድን ነገር በእርግጥ ሠራሽ አሏት። የሃሩን እኅት ሆይ! አባትሽ መጥፎ ሰው አልነበረም፤እናትሽም አመንዝራ አልነበረችም፤አሉዋት። ወደርሱም ጠቀሰች፤በአንቀልባ ያለን ሕፃን እንዴት እናናግራለን! አሉ። (ሕፃኑም) አለ፦ እኔ የአላህ ባሪያ ነኝ፤መጽሐፍን ሰጥቶኛል፣ነቢይም አድርጎኛል። በየትም ስፍራ ብኾን ብሩክ አድርጎኛል፤በሕይወትም እስከ አለሁ ሶላትን በመስገድ፣ዘካንም በመስጠት አዞኛል። ለእናቴም ታዛዥ (አድርጎኛል)፤ትዕቢተኛ እምቢተኛም አላደረገኝም። ሰላምም በኔ ላይ ነው፣በተወለድሁ ቀን በምሞትበትም ቀን፣ሕያው ሆኘ በምቀሰቀስበትም ቀን፤}[መርየም፡27-33]

ነቢዩ ዒሳ [የአላህ ሰላም በርሳቸው ላይ ይሁን] በዚህ ሁኔታ ጨቅላ ሕጻን ኾነው ተናግረዋል። ቆረይሾችም መልክተኛው ሙሐመድን  በነብይነት ከመላካቸው በፊት {እውነተኛው ታማኝ} ብለው ይጠሯቸው ነበር። ይህም በእውነተኛነታቸውና ከማንም ይበልጥ በማሕበረሰቡ ውስጥ ታማኝ የነበሩ በመሆናቸው ነው። የነብዩ  ሰብእና እና የሕይወት ታሪካቸው ትልቁ ማስረጃ በመሆኑ፣ቁርኣንም ይህን አቋማቸውን ለነብዩ እውነተኛነት አስረጅ አድርጓል። አላህ (ሱ.ወ.) እንዲህ ብሏል፦

{አላህ በሻ ኖሮ፣በናንተ ላይ ባላነበብኩትም፣(አላህ) እርሱን ባላሳወቃችሁም ነበር፤በናንተም ውስጥ ከርሱ በፊት (ምንም ሳልል) ብዙን እድሜ (አርባ ኣመት) በእርግጥ ኖሬአለሁ፤አታውቁምን?}[ዩኑስ፡16]

4- የመልክተኞችን ጥሪ መመልከት፦

ከነብይነት ጠቋሚ ማስረጃዎች መካከል መልክተኛው በጥሪው መሰረታዊ መርሆዎች ላይ ከሁሉም መልክተኞችና ነብዮች መሰረታዊ መርሆዎች ጋር አንድ መሆን አንዱ ነው። በዚህ መሰረት መልክተኛው ለአላህ (ሱ.ወ.) ተውሒድ (ለአንድነቱ) ጥሪ የሚያደርግ መሆን ይኖርበታል። ይህም፣አንድነቱን ማረጋገጥና እርሱን ብቻ ማምለክ ሰዎች የተፈጠሩበትና መልክተኞችም የተላኩበት ዐብይ ዓላማ በመሆኑ ነው። አላህ (ሱ.ወ.) እንዲህ ብሏል፦

{ከአንተ በፊትም፣እነሆ ከኔ ሌላ አምላክ የለምና ተገዙኝ በማለት ወደርሱ የምናወርድለት ቢኾን እንጂ ከመልክተኛ አንድንም አልላክንም።}[አል አንቢያእ፡25]

በተጨማሪም አላህ (ሱ.ወ.) እንዲህ ብሏል፦

{ከመልክተኞቻችንም ካንተ በፊት የላክናቸውን (ተከታላቸው)፣ከአልረሕማን ሌላ የሚገዙዋቸው የኾኑን አማልክት አድርገን እንደ ኾነ ጠይቃቸው፤}[አል ዙኽሩፍ፡45]

በተጨማሪም እንዲህ ብሏል፦

{በየሕዝቡም ሁሉ ውስጥ፣አላህን ተገዙ፣ጣዖትንም ራቁ፤በማለት መልክተኛን ልከናል፤ከነሱም ውስጥ አላህ ያቀናው ሰው አልለ፤ከነሱም ውስጥ በርሱ ላይ ጥመት የተረጋገጠበት ሰው አልለ፤በምድርም ላይ ኺዱ፤የአስተባባዮችም መጨረሻ እንዴት እንደ ነበረ ተመልከቱ።}[አል ነሕል፡36]

ሙሐመድም  ለዚህ ነው ጥሪ ያደረጉት። የአላህ መልክተኛ በወሕይ (መለኮታዊ ራእይ) ብልጫ አግኝቶ የተከበረ ቢሆንም፣እንደተቀሩት ሰዎች ሁሉ ሰብአዊ ፍጡር ነው። አላህ (ሱ.ወ.) እንዲህ ብሏል፦

{፦ እኔ፣አምላካችሁ አንድ አምላክ ብቻ ነው በማለት፣ወደኔ የሚወረድልኝ ቢጤያችሁ ሰው ብቻ ነኝ፤የጌታውንም መገናኘት የሚፈልግ ሰው፣መልካምን ሥራ ይሥራ፤በጌታውም መገዛት አንድንም አያጋራ፣በላቸው።}[አል ከህፍ፡110]

ነቢይ ለግዛትና ለሥልጣን ጥሪ አያደርግም። አላህ (ሱ.ወ.) እንዲህ ብሏል፦

{፦ ለናንተ የአላህ ግምጃ ቤቶች እኔ ዘንድ ናቸው አልልም፤ሩቅንም አላውቅም፤ለናንተም እኔ መልአክ ነኝ አልልም፤ወደኔ የሚወርድልኝን እንጅ ሌላን አልከተልም በላቸው፤ዕውርና የሚያይ ይተካከላሉን? አታስተነትኑምን? በላቸው።}[አል አንዓም፡50]

ለሕዝቡ ለሚያቀርበው ጥሪና ለትምሕርቱም ዋጋ እንዲከፈለው አይጠይቅም። አላህ (ሱ.ወ.) ነቢዮቹ ኑሕ፣ሁድ፣ሳሊሕ፣ሉጥና ሹዐይብ የተናገሩትን አንዲህ ሲል ገልጾልናል፦

{በርሱም ላይ ምንም ዋጋ አልጠይቃችሁም፤ዋጋዬ በዓለማት ጌታ ላይ እንጅ በሌላ ላይ አይደለም።}[አልሹዐራ፡109፣127፣145፣164 እና 180]

ሙሐመድም  ለሕዝባቸው እንዲህ ብለዋል፦

{በላቸው፦ በርሱ ላይ ምንም ዋጋ አልጠይቃችሁም፤እኔም ከተግደርዳሪዎቹ አይደለሁም።}[ሷድ፡86]

5- የአላህ ረድኤትና እገዛ የተሰጣቸው መሆኑ፦

ለነቢያትና መልክተኞች እውነተኛነት ማረጋገጫ ከሆኑት አስረጅዎች አንዱ የአላህ ረድኤትና እገዛ የተቸራቸው መሆኑ ነው። ይህም አንድ ግለሰብ በውሸት የአላህ ነብይና መልክተኛው ነኝ ብሎ ጥሪው በማሰራጨት ላይ ከአላህ ረድኤት እገዛና ድል ይሰጠዋል ብሎ ማሰብ የማይቻል በመሆኑ ነው። ይልቅዬ ቁጣና ቅጣት ይወርድበታል ተብሎ ነው የሚጠበቀው!! አላህ (ሱ.ወ.) እንዲህ ብሏል፦

{በአላህም ላይ ውሸትን ልትቀጣጥፉ፣ምላሶቻችሁ በሚመጥኑት ውሸት፦ ይህ የተፈቀደ ነው፤ይህም እርም ነው፣አትበሉ፤እነዚያ በአላህ ላይ ውሸትን የሚቀጣጥፉ፣አይድኑም።}[አል ነህል፡116]

በተጨማሪም እንዲህ ብሏል፦

{በኛ ላይም ከፊልን ቃላት (ያላልነውን) በpAUpAUvAUUAUpAUpAUpAU(የተንጠለጠለበትን ጅማት) በቆረጥን ነበር።}[አልሓቃህ፡44-46]