የሕግና ድንጋጌ አወጣጥ መሰረቶች

የሕግና ድንጋጌ አወጣጥ መሰረቶች

እስላማዊው ሸሪዓ ለሰው ልጆች ሁሉ በየትኛውም ዘመንና ስፍራ ተስማሚ እንዲሆን የሚያደርጉት መሰረቶችና መደላድሎች አሉት። ከነዚህም መካከል የሚከተሉትን እናገኛለን፦

አንደኛ - ገርነትና ችግር አስወጋጅነት፦

ሁሉም ሸሪዓዊ ግዴታዎች ኃላፊነቱ ከሚመለከታቸው ሰዎች አቅምና ችሎታ በላይ የሚሆኑ አይደሉም። ሃይማኖቱ ገር በመሆኑ ከተለመዱ ሥራዎች ተለይተው ለአፈጻጸም አስቸጋሪ የሆኑ ነገሮች የሉበትም። አላህ (ሱ.ወ.) እንዲህ ብሏል፦

{አላህ በናንተ ገሩን (ነገር) ይሻል፤በናንተም ችግሩን አይሻም፤}[አልበቀራህ፡185]

በተጨማሪም አላህ (ሱ.ወ.) እንዲህ ብሏል፦

{አላህ ከናንተ ሊያቃልልላችሁ ይሻል። ሰውም ደካማ ኾኖ ተፈጠረ።}[አልኒሳእ፡28]

በተጨማሪም አላህ (ሱ.ወ.) እንዲህ ብሏል፦

{አላህ ነፍስን ከችሎታዋ በላይ አያስገድድም፤}[አልበቀራህ፡185]

ከዓእሻ (ረ.ዐ.) በተላለፈው መሰረት ፦ ‹‹ነቢዩ  ሁለት አማራጮች ሲቀርብላቸው ኃጢአት እስከሌለበት ድረስ ቀለል ያለውን እንጅ አይመርጡም ነበር፤ኃጢአት ካለበት ግን ከማንም በላይ ከርሱ ይርቁ ነበር። በአላህ እምላለሁ፣የአላህ ሕግ ተጥሶ የሚበቀሉ እስካልሆነ ድረስ በምንም ነገር ራሳቸውን በተመለከተ ማንንም ሰው ተበቅለው አያውቁም።›› [በቡኻሪ የተዘገበ] (36)

ከእስላማዊ ሕግ ችግር ማስወገጃና ገርነት ገጽታዎች አንዱ ድካምና አታካችነት ሳይኖርበት አማኙ ግዴታዎቹን በቀላሉ ይወጣ ዘንድ ግዴታዎቹ ገርና ቀላል መሆናቸው አንዱ ነው። አድካሚነትና አስጨናቂነት አለመኖሩን ሲገልጽ አላህ (ሱ.ወ.) እንዲህ ብሏል፦

{በናንተም ላይ በሃይማኖቱ ውስጥ ምንም ችግር አላደረገባችሁም፤}[አልሐጅ፡78]

የታዘዙ ግዴታዎች ዓላማቸው በዚህች ሕይወትና በወዲያኛው ዓለም ሕይወት ሰውን ወደ መታደልና ወደ ደስተኝነት ሕይወት ማድረስ እንደመሆኑ፣ሕግጋቱ የመጡት የሰው ልጅ ተፈጥሮ ሊሸከመውና በቀላሉ ሊወጣው በሚችለው ተገቢ ተመጣጣኝ ሁኔታ ብቻ ነው። አላህ (ሱ.ወ.) እንዲህ ብሏል፦

{እላንተ ያመናችሁ ሆይ! ለናንተ ቢገለጹ ከሚያስከፏችሁ ነገሮች አትጠይቁ፤ቁርኣንም በሚወርድበት ጊዜ ከርሷ ብትጠይቁ፣ለናንተ ትገለጻለች፤ከርሷ (ካለፈው ጥያቄያችሁ) አላህ ይቅርታ አደረገ፤አላህም መሓሪ ታጋሽ ነው። ከናንተም በፊት ሕዝቦች በእርግጥ ጠየቋት፤ከዚያም በርሷ (ምክንያት) ከሓዲዎች ኾኑ።}[አልማእዳህ፡101-102]

ሁለተኛ - የሰው ልጆችን ጥቅሞች ግንዛቤ ውስጥ ማስገባቱ፦

የእስላምን ሸሪዓዊ ድንጋጌዎች ተከታትሎ ያስተዋለ ሰው፣ዓላማቸው የሰው ልጆችን ጥቅምና ቅን ፍላጎቶች በግልም ሆነ በጋራ በሁሉም ዘመንና ስፍራ እውን የሚያደርግ፣በዚህ ዓለምና በወዲያው ዓለም ሕይወቱ መጥፎና እኩይ የሆነውን ሁሉ የሚያስወግድ መሆኑን ይገነዘባል። አላህ (ሱ.ወ.) እንዲህ ብሏል፦

{(ሙሐመድ ሆይ!) ለዓለማትም እዝነት አድርገን እንጅ አልላክንህም።}[አል አንቢያ፡107]

የነቢዩ ሙሐመድ  መላክ የሰው ልጆችን ጥቅሞች እውን ለማድረግ የታቀደ እዝነትና ጸጋ ሲሆን፣ይህ ባይኖር ኖሮ ነቢዩ  በእዝነትና በርህሩህነት ባልተገለጹ ነበር። ከአላህ የታዘዙ ግዴታዎች ሁሉ መነሻና መድረሻቸው የሰው ልጆች መንፈሳዊና ቁሳዊ ጥቅሞች ናቸው። አላህ (ሱ.ወ.) ከባሮቹ ምንም የማይፈልግ በራሱ የተብቃቃ ጌታ ነውና የሰዎች በጎ ሥራ አይጠቅመውም፤ክፉ ሥራቸውም አይጎዳውም። የሸሪዓ ሕጉም በጥቅሉ ፍትሕ ነው፤በጥቅሉ እዝነትና ርህራሄ ነው፤በጥቅሉ ጠቀሜታ ነው፤በጥቅሉ ጥበብ ነው። ከፍትሕ ወደ ግፍ፣ከእዝነት ወደ ጭካኔ፣ከጥቅም ወደ ጉዳት፣ከጥበብ ወደ ከንቱነት የወጣ ነገር ሁሉ የሸሪዓው አካል አይደለም።

ሦስተኛ - በሁሉም መልኩ ፍትሕን እውን ማድረግ፦

ፍትሕን እውን ማድረግና ማጽናትን መሰረታዊ አጠቃላይ መርሕ የሚያደርጉ ቁርኣናዊ አንቀጾች በርካታ ናቸው። አንዳንዶቹ ለፍርድ ማስተካከልና ለፍትሕ ማስፈን ጥሪ የሚያደርጉ ሲሆኑ፣ሌሎቹ ደግሞ በተቃራኒ ወገን ላይ እንኳ ቢሆን ግፍና በደልን መፈጸም የሚያጥላሉና የሚያወግዙ ናቸው። አላህ (ሱ.ወ.) እንዲህ ብሏል፦

{እላንተ ያመናችሁ ሆይ! ለአላህ ቀጥተኞች፣በትክክል መስካሪዎች ኹኑ፤ሕዝቦችንም መጥላት፣ባለማስተካከል ላይ አይገፋፋችሁ፤አስተካክሉ፤(ማስተካከል) ለአላህ ፍራቻ የቀረበ ነው። አላህንም ፍሩ። አላህ በምትሠሩት ሁሉ ውስጠ ዐዋቂ ነው።}[አልማእዳህ፡8] (38)

አራተኛ - አጠቃላይነትና አንዱ ሌላውን የሚያሟላ መሆኑ፦

የአንድን ሃይማኖትና መልክት ትክክለኛነት ከሚያመለክቱ አበይተ ነገሮች አንዱ የተለየ የአጠቃላይነትና አንዱ ሌላውን የሚያሟላበት ልዩ መለያ ያለው መሆኑ ነው። አላህ (ሱ.ወ.) እንዲህ ብሏል፦

{በመጽሐፉ ውስጥ ምንም ነገር [ሳንገልጽ] አልተውንም።}[አል አንዓም፡38]

በተጨማሪም እንዲህ ብሏል፦

{መጽሐፉንም፣ለሁሉ ነገር አብራሪ፣መሪም እዝነትም፣ለሙስሊሞችም አብሳሪ ኾኖ ባንተ ላይ አወረድነው።}[አል ነሕል፡89]

ይህ አጠቃላይነት በዐቂዳው (በእምነት)፣በአመለካከት፣በዕባዳ (አምልኮተ አላህ) እና በጽድቅ ሥራ፣በስነምግባርና በሰናይ ተግባራት፣በሕግ አወጣጥ፣በቅንብርና በአገዛዝ ሥርዓት፣በሁሉም የሕይወት ፈርጆች ውስጥ የሚንጸባረቅ ነው።

አምስተኛ - ተመጣጣኝነት ሚዘናዊነትና መካከለኛነት፦

የእስላም ሃይማኖት የተመጣጣኝነት የሚዛናዊነትና የመካከለኛነት ሃይማኖት ነው። አላህ (ሱ.ወ.) እንዲህ ብሏል፦

{እንደዚሁም (እንደ መራናችሁ) . . ምርጥና ሚዘናዊ ሕዝቦች (ኡመት) አደረግናችሁ፤}[አል በቀራህ፡143]

በሕግጋቱና በሥርዓቱ ውስጥ ያለው ማንኛውም ነገር በተራቀቀ ሚዘናዊነት የተዘጋጀ ነው። አላህ (ሱ.ወ.) እንዲህ ብሏል፦

{ሰማይንም አጓናት፤ትክክለኛነትንም [ፍትሐዊነትንም] ደነገገ።}[አልረሕማን፡7]

አላህ (ሱ.ወ.) ሙስሊሞችን በሁሉም ነገር ሚዘናዊ እንዲሆኑ ያዘዘ ሲሆን ከዚህ ውስጥ የሚከተለውን የአላህ (ሱ.ወ.) ቃል እናገኛለን፦

{እነዚያም፣በለገሱ ጊዜ የማያባክኑት፣የማይቆጥቡትም ናቸው፤በዚህም መካከል (ልግስናቸው) ትክክለኛ [ሚዛናዊ] የኾነ ነው።}[አልፉርቃን፡67]

ነቢዩም  ማክረርንና ጫፍ ረጋጭነትን ሲከለክሉ እንዲህ ብለዋል፦ ‹‹በሃይማኖት ጉዳይ ከልክ አልፎ ከማክረር ራቁ፣ከናንተ በፊት የነበሩትን ያጠፋው ከልክ ያለፈ አክራሪነት ነውና።›› ለተመጣጣኝነትና ለሚዘናዊነት ሲያዙም ነቢዩ  እንዲህ ብለዋል፦ ‹‹ለጌታህ መፈጸም ያለበት ግዴታ አለብህ፤ለገዛ ራስህም መፈጸም ያለበት ግዴታ አለብህ፤ለባለቤትህም መፈጸም ያለበት ግዴታ አለብህ፤እናም ለሁሉም ተገቢና ተመጣጣኝ መብቱን ስጥ።››