የአለማመን ወይስ የሃይማኖት መንገድ?!

የአለማመን ወይስ የሃይማኖት መንገድ?!

የአለማመን ወይስ የሃይማኖት መንገድ?!

ሰዎች ከላይ ለተጠቀሱ ጥያቄዎች ምላሽ ለመስጠት በመጀመሪያ በሁለት መንገዶች ያስባሉ። አምላክ የለም፣ዩኒቨርስ ቁስ አካል ብቻ ነው በሚለው የኤቲዝም መንገድና አላህ የሁሉም ነገሮች ፈጣሪ ጌታ ነው ብሎ በሚያምነው መንገድ ያስባሉ። ከዚህ በመንደርደር በርካታ ጥያቄዎች ይነሳሉ፦

-ይህ ዩኒቨርስ ተለይቶ የተወሰነለት ጊዜ ሳይኖረው በአጋጣሚ በተከሰቱ መስተጋብሮች እንዳው ራሱን በራሱ ሊያስገኘኝ ይችላልን?!

-ይህ ዓይነቱ የዕውር ድንብር አጋጣሚ በተራቀቀ ሥርዓት የተቀነባበረውን ዓለም ፈጠረ ብሎ ማሰብ ቻላልን?!!

 

-የሰው ልጅ በዘመናት ታሪኩ ውስጥ የደረሰበት ደረጃ በአዝጋሚ ለውጥ ወይም በአጋጣሚ የተገኘ ነውን?! እኛም በአጋጣሚና በሥርዓተ አልበኝነት የሚያነዳ ነፋስ የሚያሽከረክራት ቅንጣት ጥጥ እንጅ ምንም አይደለንም ማለት ነውን?

-የሰው ልጅ፣ሕግ አውጭ አምላክ፣ጥበበኛ ፈጣሪና ሁሉም ነገር እርሱ ብቻ ከርሱ ወዲያ ምንም ነውን?!

-ከስሜታዊ ግንዛቤ በላይ የሆነው ሜታፊዚካዊው ዓለም ከሞገደኛው ኢ-አማኝነትና ከተጨባጩ ዓለም ፊት መጥፋት ያለበት ሕልውና የሌለው ሲሪብዱ እንጂ ሌላ ምንም አይደለም ማለት ነውን?!

-የሰው ልጅ ከማንኛውም ነገር ነጻ የሆነ ቁስ አካል ብቻ ወይም ሥር መሠረቱ በጊዜ ሂደት አዝጋሚ ለውጥ የተፈጠረ ዝንጀሮ ነውን?!

እንዲህ ያሉ የመጠቁ ባሕርያት፣የተራቀቁ ስነ ምግባራትና አስደናቂ አወቃቀር ያሉትን ክቡሩን የሰውን ልጅ፣ግዑዝ ቁስ አካል እንዴት ሊፈጥረው ይችላል? ለራሱ የሌለውን ለሌላ እንዴት ሊሰጥ ይችላል?

-ይህች ዓለማዊ ሕይወት የሰው ልጅ የመጨረሻ ግብና የምኞቶቹ ዲካ ነች፤ስለዚህም መለኮታዊ ሃይማኖቶች ከሰው በላይ ሌላ ኃይልል ስለመኖሩና ከዚህ ሕይወት ውጭ ሌላ ሕይወት ስለመኖሩ የተናገሩት ሁሉ ግምት የሚሰጠው አይደለም ማለት ነውን?

አላህ (ሱ.ወ) እንደዚያ ለሚያስቡት እንዲህ ብሏል፦

{እርሷም (ሕይወት) የቅርቢቱ ሕይወታችን እንጅ ሌላ አይደለችም፤እንሞታለን፤ሕያውም እንኾናለን (ከፊላችን ሲሞት ከፊላችን ሕያው ይኾናል፣ይተካል) ከጊዜም (ማለፍ) በስተቀር ሌላ አያጠፋንም አሉ፤ለነርሱም በዚህ (በሚሉት) ምንም ዕውቀት የላቸውም፤እነርሱም የሚጠራጠሩ እንጅ ሌላ አይደሉም።}[አልጃሢያ፡24]

የካዱ ሰዎችን አስመልክቶ አላህ (ሱ.ወ) እንዲህ ይላል፦

{ነፍሶቻቸውም ያረጋገጧት ሲኾኑ ለበደልና ለኩራት በርሷ ካዱ፤የአመጸኞችም ፍጻሜ እንዴት እንደ ነበረ ተመልከት።}[አልነምል፡14]

ኤቲስቶች ትንሽም ይሁን ትልቅ የማንኛውንም ፍጡር የሕይወት ምስጢር ምንነት ፈጽሞ ማወቅ አለመቻላቸውን አምነው ይቀበላሉ። ሕይወት ያለውን ነገር አንዴ ከሞተ በኋላ መልሶ ሕያው ማድረግ እንደማይችሉም እንደዚሁ አምነው ይቀበላሉ። ታድያ ይህን ዩኒቨርስ ያስገኘ ነው ብለው ብዙ የሚያወሩለት ቁስ አካል የት ገባ?! አካል በድን ቁስ አካል ከሆነ በኋላ ሕይወትን መልሶ እንዲዘራበት ቁስ አካልን ለምን አይማጸኑትም?

ኤቲስቶች እንደሚሉት ሃይማኖት ባዶ ቅዠት ቢሆን ኖሮ የሰው ልጆች እስከዚህ ደረጃ ሃይማኖትን በማክበር ላይ እንዴት ሊስማሙ ቻሉ? ነብዮች ለዘመናት ለምንድነው ስኬታማ የሆኑትና ያወረሱት ትምህርት በሰዎች ልብ ውስጥ ሕያው ሆኖ የቀጠለው። በአንጻሩ ግን የሌሎች ሰዎች አስተሳሰቦች ለዘመናት መሞትና መረሳት ብቻ ሳይሆን ባለቤቶቹ የተዋጣላቸው ተናጋሪዎች ከመሆናቸውም ጋር አሰልቺ የሚሆኑት ለምንድነው?! በጎ የሚሠራውን ክፉ ከሚሠራው መለየት እንዴት ነው የሚቻለው? ወንጀለኛን ከወንጀል ድርጊቱ እንዲታቀብ የሚያደርገውስ ማነው? የሀብታሙን ልብ ለደሃው እንዲራራ የሚያደርገውስ ማነው? ሌባን አጭበርባሪን፣እምነት አጉዳይን፣የአደንዛዥ እጽ ተጠቃሚን . . እነዚህን ሁሉ ፍላጎታቸውን እውን እንዳያደርጉ የሚከለክላቸው ማነው?

ኤቲዝም የተንሰራፋባቸው ህብረተሰቦች በእርስ በርስ በደል፣በራስ ወዳድነት፣በሥጋዊ ፍላጎት ተገዥነትና በሌሎቹም እኩይ ተግባራት የተኩላዎች መንጋ በሚኖርበት ሁኔታ ይኖራሉ። በመሆኑም ኤቲዝም ለአስከፊ ሁኔታ፣ለአለመታደል፣ለድህነት፣እየጨመረ ለሚሄደው ጭንቀትና አለመረጋጋት ከዋነኞቹ ምክንያቶች አንዱ ነው። አላህ (ሱ.ወ) እንዲህ ብሏል፦

{ከግሣጼም የዞረ ሰው፣ለርሱ ጠባብ ኑሮ አልለው፤በትንሣኤም ቀን ዕውር ኾኖ እንቀሰቅሰዋለን።}[ጣሃ፡124]

ኤቲዝም አእምሮ፣ሎጂክም ሆነ የሰው ልጅ ተፈጥሮ የማይቀበለው ብልሹ አስተሳሰብ ነው። ሳይንስን የሚጻረር በመሆኑም ብዙ ሳይንቲስቶች ውድቅ ያደርጉታል። ይህን በእጹብ ድንቅ ሥራ የተፈጠረውን ዩኒቨርስ ባልታወቀ አጋጣሚ ተገኘ ብሎ ስለሚያምን ሕይወት ውስጥ ሎጂክ የለም በሚል መነሻ ላይ የተመሰረተ በመሆኑ ከስነ አስተሳሰብ ጋር ይጻረራል። ጤናማ ተፈጥሮ ኢአማኝ ነን በሚሉት ዘንድ እንኳ ለሃይማኖት ጥሪ የሚያደርግ በመሆኑ ኤቲዝም ከትክክለኛ ሰብአዊ ተፈጥሮ ጋርም ይጋጫል።

{ነፍሶቻቸውም ያረጋገጧት ሲኾኑ ለበደልና ለኩራት በርሷ ካዱ፤የአመጸኞችም ፍጻሜ እንዴት እንደ ነበረ ተመልከት።}[አል ነምል፡14]

ጥያቄዎቹ አሁንም ምላሽ ይሻሉ!!

የሰው ልጅ የነዚህን ጥያቄዎች ምላሽ በገዛ ራሱ ብቻ ለማወቅ የሚያደርገው ጥረት ከንቱ ነው። መሰል ጉዳዮች በሃይማኖት ክልል ውስጥ የሚገቡ በመሆናቸው፣ዘመናዊው ሳይንስ ከነዚህ ጥያቄዎች ለአንዱ እንኳ ምላሽ መስጠት አልቻለም። በዚህም ምክንያት በጥያቄዎቹ ዙሪያ የተለያዩ ዘገባዎች፣በርካታ ውዥንብሮችና አፈተረቶች፣በሰው ላይ ግርታና ጭንቀትን በሚያባብስ ሁኔታ ሲናፈሱ ይስተዋላሉ። በመሆኑም የሰው ልጅ አላህ ወደ ደህንነትና እርጋታ፣ወደ መታደልና ደስተኝነት መዳረሻ ወደሚያደርሰው ትክክለኛው መንገድ ካልመራው በስተቀር፣ለነዚህ ጥያቄዎች አጥጋቢና በቂ መልስ ማግኘት አይቻለውም።

እነዚህ ጉዳዮችና ጥያቄዎች ከሰው ልጅ ሕዋሳዊ ግንዛቤ በላይ ከሆኑ ነገሮች ውስጥ የሚቆጠሩ በመሆናቸው በነዚህና በመሰል ጉዳዮች ላይ መወሰን የሚችሉት ሃይማኖቶች ብቻ ናቸው። በብቸንነት እውነታውን መንገርና ሐቁን ማሳወቅ የሚችለውም፣አላህ ወደ ነብዮቹና ወደ መልክተኞቹ ያስተላለፈው እውነተኛው ሃይማኖት ብቻ ነው። አላህ (ሱ.ወ) እንዲህ ብሏል፦

{የአላህ መመራት (ትክክለኛው) መመራት እርሱ ብቻ ነው በላቸው፤} [አል በቀራህ፡120]

አላህ (ሱ.ወ) እንዲህ ብሏል፦

{መምሪያው የአላህ መምሪያ ብቻ ነው በላቸው፤} [ኣል ዒምራን፡73]

ስለዚህም እውነተኛውን ሃይማኖት መፈለግ፣መማርና በርሱ ማመን የሰው ልጅ ግዴታ ይሆናል። በዚህም ነው ግራ መጋባትና ጥርጣሬዎች ተወግደውለት፣ወደ ቀጥተኛው የአላህ መንገድና ወደ መታደልና መረጋጋት መንገድ የሚመራው።

ታዲያ መልሶቹ እንዴት ነው የሚሆኑት?!

አላህ (ሱ.ወ) እንዲህ ብሏል፦

{በእርግጥም ሰውን ከነጠረ ጭቃ ፈጠርነው። ከዚያም በተጠበቀ መርጊያ ውስጥ የፍቶት ጠብታ አደረግነው። ከዚያም ጠብታዋን (በአርባ ቀን) የረጋ ደም አድርገን ፈጠርን፤የረጋውንም ደም ቁራጭ ሥጋ አድርገን ፈጠርን፤ቁራጭዋንም ሥጋ አጥንቶች አድርገን ፈጠርን፤አጥንቶቹንም ሥጋን አለበስናቸው፤ከዚያም (ነፍስን በመዝራት) ሌላ ፍጥረትን አድርገን አስገኘነው፤ከሰዓሊዎችም ሁሉ በላጭ የኾነው አላህ ላቀ። ከዚያም እናንተ ከዚህ በኋላ በእርግጥ ሟቾች ናችሁ። ከዚያም እናንተ በትንሣኤ ቀን ትቀሰቀሳላችሁ።}[አል ሙእምኑን፡12-16]

እናም የመጨረሻው መጣፊያ መንቃትና ወደ አላህ መመለስ ብቻ ነው። አላህ በከንቱ ከመፍጠር የላቀ ነውና ይህ ፍጥረት ለታላቅ ጥበብና ምስጢር እንጅ ከቶም ለከንቱ አልነበረም። አላህ (ሱ.ወ) እንዲህ ብሏል፦

{የፈጠርናችሁ ለከንቱ መኾኑን እናንተም ወደኛ የማትመለሱ መኾናችሁን ጠረጠራችሁን? (ለከንቱ የፈጠርናችሁ መሰላችሁን?)።}[አል ሙእምኑን፡24]

እናም አላህ ጋኔንና ሰውን እርሱን ብቻ ያለ ምንም ማጋራት እንዲያመልኩትና እንዲገዙት እንጂ ለከንቱ አልፈጠራቸውም። አምልኮውም በተሟላ ትርጉሙና ጽንሰ ሀሳቡ፣ግዴታዎችን፣ሶላትና ውዳሴን (ዝክርን)፣ምድርን ማልማት፣ለሰው ልጆች መጥቀምን የመሳሰሉና አላህ የሚወዳቸውን ነገሮች ሁሉ በመፈጸም የሚገለጽ አጠቃላይ ዘት ያለው አምልኮ ነው። አላህ (ሱ.ወ) እንዲህ ብሏል፦

{ጋኔንንና ሰውንም ሊግገዙኝ እንጅ ለሌላ አልፈጠርኳቸውም።}[አል ዛርያት፡56]

መላው የሰው ልጅና ፍጥረታት በሙሉ ወደርሱ ተመላሾችና መጨረሻቸውም ወደርሱ ብቻ ነው ።አላህ (ሱ.ወ) እንዲህ ብሏል፦

{መመለሻም ወደ አላህ ብቻ ነው።}[ኣል ዒምራን:28]

ይህ የተረጋገጠ እውነታ ከሰው ልጅ ሕይወት ውስጥ ከንቱነትን ያስወገዳል፤ለሕይወታቸው ትርጉም በመስጠትም የሕሊና ደስታና መረጋጋትን ያጎናጽፋቸዋል። አላህ (ሱ.ወ) እንዲህ ብሏል፦

{ወይስ ያለ አንዳች (ፈጣሪ) ተፈጠሩን? ወይስ እነርሱ ፈጣሪዎች ናቸው? ወይስ ሰማያትንና ምድርን ፈጠሩን? አይደለም አያረጋግጡም።}[አል ጡር፡35-36]

የሰው ልጅ የዚህን ዩኒቨርስ ምስጢር ማወቅ ተስኖት ደካማ ሆኖ በሚቆምበት ጊዜ፤በአላህ ፍጥረታት፣በምድሩ፣በከዋክብቱና በተቀሩት ጠፈራዊ አካላት፣በቀንና ሌሊት መተካካት፣በሕይወትና በሞት . . በዚህ ዩኒቨርስ ውስጥ አላህ ስለ አስገኛቸው ፍጥረታት በጥቅሉ አስተውሎ ያስተነትናል። ይህን ካደረገ ከርሱ ይበልጥ ኃያል የሆነ፣ሊገዛውና ሊታዘዘው የሚገባ፣ምንዳውን የሚከጅልና ቅጣቱን የሚፈራ ኃያል የሆነ ፈጣሪ አምላክ መኖሩን በተፈጥሮው አውቆ ያረጋግጣል። በዚህ ሁኔታ ዩኒቨርስን ማስተንተን ኃያል ቻይና ጥበበኛ የሆነ ፈጣሪ ስለመኖሩ፣ቁስ አካል ካለመኖር በኋላ ወደ መኖር የመጣ ከፍጥረታቱ ውስጥ አንዱ ፍጡር እንጅ ሌላ አለመሆኑን አምኖ ይቀበላል።

ይህን ራሱን ለፍጡራን አገልጋዮቹ ያስተዋወቀው፣ጥራት ይገባውና ከዚህ የተብቃቃ እየሆነ አንቀጾቹንና ምልክቶቹን ምስክርና ማስረጃ አድርጎ የሰጣቸውን፣ራሱን በምሉእ ባህርያት የገለጸውን ጥበበኛ ቻይ አምላክ፣ሕልውናውን፣ጌታነቱንና አምላክነቱን መለኮታዊ ሃይማኖቶች፣አስገዳጅ አእምሯዊ እሳቤና ጤናማ ተፈጥሮ ያረጋገጡ ሲሆን ሕዝቦች ሁሉ በሙሉ ድምጽ ይስማሙበታል።