የስልጣኔ መንገድ መደላደሎች

የስልጣኔ መንገድ መደላደሎች

እስላማዊው ስልጣኔ ግን ጉልህ በሆኑ መለያዎቹና ልዩ በሆኑ ባሕርያቱ ሌሎች ስልጣኔዎች የሚጋሩት የተወሰኑ ጉዳዮች ቢኖሩም የስልጣኔ መሰረትቶችን፣ግቦቹንና መርሆዎቹን በተመለከተ የራሱ የሆነ ነጻ ገጽታዎችና መገለጫዎች ያሉት ምሉእ ማንነት ያለው ስልጣኔ ነው።

የእስላም ስልጣኔ መሰረት፣በግሪኮች ዘንድ እንዳለው ዓይነት አእምሮን ከገደብ ባለፈ ሁኔታ አግንኖ ማምለክ አይደለም። ሮማውያን ዘንድ እንደ ነበረው በስልጣን፣በኃይልና በተጽእኖ አምላኪነት ላይ የተመሰረተም አይደለም። በፋሪሳውያን ዘንድ እንደ ነበረው በሥጋዊ ደስታዎች፣በብርቱ ጦረኝነትና በፖለቲካዊ አቅም ላይ የሚያተኩርም አይደለም። በሕንዶችና በከፊል ቻይናውያን ዘንድ እንደ ነበረው በመንፈሳዊ ኃይል በመመካት ላይ የታነጸም አይደለም። በመካከለኛው ክፍለ ዘመን አውሮፓን ለድቅድቅ የማይምነት ጨለማ በዳረገውና በአፈ ታሪክና በቅዠት ላይ የተመሰረተው የመነኮሳትና የካህናት የእብሪት ኃይልና ተጽእኖ ላይ የተመረኮዘም አይደለም። ከግሪክና ከሮማውያን ስልጣኔ እንደ ተወረሰውና በቁሳዊ ዕውቀት ላይ በመመካት የምድረ ዓለሙን እምቅ ሀብት በመዝረፍ ላይ እንደ ቆመው ዘመነኛው የአውሮፓ ስልጣኔም አይደለም። እሰላማዊ ስልጣኔ የተመሰረተው በተውሒድ፣በርእዮት፣ሰብአዊ ክብርን በማረጋገጥና ሁሉንም የሰው ልጅ የሕወት ፈርጆች በሚዳስስ እውነታ ላይ ነው። በዚህም እስላማዊው ስልጣኔ ራሱን የቻለና የተሟላ፣አጠቃላይነት ያለው ሕግና ሥርዓት ባለቤት የሆነ፣ከተቀሩት ሌሎች ስልጣኔዎች መርሆዎች ጋር መሰረታዊ የሆነ ልዩነት ያለው ስልጣኔ ነው። እስላማዊው ስልጣኔ እውስጡ በያዘው የትግልና የተጋድሎ፣የፍትሕና የርትዕ፣ከተቃራኒ ጋር ተቻችሎ በመኖር፣ለመላው የሰው ዘር ደግ ደጉን በመውደድና በመስራት፣ዕውቀትና ጥበብን በማሰራጨት . . ረገድ ባለው እምቅ ኃይልና የመንፈስ ጥንካሬ በሌሎች ላይ የበላይነትን የተቀዳጀ ስልጣኔ ነው። ስለሆንም በእጁ ካለው ታላቅ ጥሪትና እምቅ ስንቅ አንጻር ዳግም የሰው ልጆችን አመራር ለመረከብ የታጨ ድንቅ ስልጣኔም ነው።

እስላማዊ ስልጣኔ የራሱ የሆኑ አያሌ መለያዎችና መገለጫዎች አሉት፤ከነዚህም መካከል የሚከተሉት ይገኛሉ፦

1-ኢማንና ተውሒድ ፦

ኢማን የደስተኝነት መንገድ ስረ መሰረትና ለዕውቀት ግብይትና ለስልጣኔ ምስረታ ዋነኛው ግፊት ፈጣሪ ተደርጎ ይወሰዳል። በአላህ በማመንና አንድነቱን በማረጋገጥ ላይ ያልተመሰረተ ማንኛውም ስልጣኔ፣በውስጣዊ ቅራኔና ግጭት የታጨቀ፣እርሱ በርሱ አንዱ ክፍል ሌላውን የሚያፈርስ፣የሰውን ልጅ ሕይወት በማበላሸት ወደ አለመታደል የሚወስዱትና የተለያዩ ስሞች ተሰጥቷቸው የሚመለኩ አማልክት የሚመለኩበት ስልጣኔ ነው!! አላህ (ሱ.ወ.) እንዲህ ብሏል፦

{በሁለቱ (በሰማያትና በምድር) ውስጥ ሌላ አማልክት በነበሩ ኖሮ፣በተበላሹ ነበር፤የዐርሹ ጌታ አላህም ከሚሉት ሁሉ ጠራ።}[አል አንቢያ፡22]

በተጨማሪም አላህ (ሱ.ወ.) እንዲህ ብሏል፦

{አላህ ምንም ልጅን አልያዘም (አልወለደም)፤ከርሱም ጋር አንድም አምላክ የለም፤ያን ጊዜ፣(ሌላ አምላክ በነበረ)፣አምላክ ሁሉ በፈጠረው ነገር በተለየ ነበር፤ከፊላቸውም በከፊሉ ላይ በላቀ ነበር፤አላህ ከሚመጥኑት ሁሉ ጠራ።}[አል ሙእሚኑን፡91]

በተጨማሪም (ሱ.ወ.) እንዲህ ብሏል፦

{(ሙሐመድ ሆይ) በላቸው ፦ እንደምትሉት ከርሱ ጋር አማልክት በነበሩ ኖሮ ያን ጊዜ ወደ ዐርሹ (ወደ ዙፋኑ) ባለቤት መንገድን በፈለጉ ነበር።} [አል እስራእ፡42]

የዚህ ነፀብራቅ በብዙዎቹ ስልጣኔዎች ላይ የደረሰውና በመድረስ ላይ የሚገኘው ሲሆን፣መድረስ ከፈለጉበት ግባቸው ተዛንፈው፣ዓላቸውን ስተው በጎ አስበው ቢሆን እንኳ ለሰው ልጆች ያለመታደልና ለጥፋት መንስኤ ሆነዋል። አላህ (ሱ.ወ.) እንዲህ ብሏል፦

{ከርሱ በቀር ሌላ አምላክ የሌለውን አንድን አምላክ ሊግገዙ እንጂ ያልታዘዙ ሲኾኑ፣ሊቃውንቶቻቸውንና መነኮሳታቸውን፣የመርየምን ልጅ አልመሲሕንም፣ከአላህ ሌላ አማልክት አድርገው ያዙ፤ከሚያጋሩት ሁሉ ጠራ ነው።}[አል ተውበህ፡31]

2-ዓለም አቀፋዊነት ፦

እስላም ለሁሉም ዘመንና ስፍራ፣ለሁሉም የሰው ዘርና ቋንቋ፣ለሁሉም የቆዳ ቀለምና ዝርያ የመጣ ዓለም አቀፋዊ ሃይማኖት ነው። አላህ (ሱ.ወ.) እንዲህ ብሏል፦

{አንተንም ለሰዎች ሁሉ በመላ፣አብሳሪና አስፈራሪ አድርገን ቢኾን እንጂ አልላክንህም፤ግን አብዛኞቹ ሰዎች አያውቁም።}[ሰበእ፡28]

በተጨማሪም አላህ (ሱ.ወ.) እንዲህ ብሏል፦

{ያ ፉርቃንን (ውነትን ከውሸት የሚለየውን መጽሐፍ፣ቁርኣንን) በባሪያው ላይ፣ለዓለማት አስፈራሪ [አስጠንቃቂ] ይኾን ዘንድ ያወረደው (አምላክ)፣ክብርና ጥራት ተገባው።}[አል ፉርቃን፡1]

በተጨማሪም አላህ (ሱ.ወ.) እንዲህ ብሏል፦

{(ሙሐመድ ሆይ!) በላቸው ፦ እላንተ ሰዎች ሆይ! እኔ ወደናንተ ወደ ሁላችሁም የአላህ መልክተኛ ነኝ፤(እርሱም) ያ የሰማያትና የምድር ንግሥና ለርሱ ብቻ የኾነ ነው፤}[አል አዕራፍ፡158]

በተጨማሪም (ሱ.ወ.) እንዲህ ብሏል፦

{(ሙሐመድ ሆይ!) ለዓለማትም እዝነት አድርገን እንጅ አልላክንህም።}[አል አንቢያ፡107]

እስላም የመጣው በሁኔታዎች መለዋወጥ የማይለወጥ ቋሚ ዐቂዳ፣በሁሉም ዘመንና ስፍራ ከሰው ልጅ ተፈጥሮ ጋር የተጣጣመ የፍትሕ፣ የእውነትና የበጎነት መርህ ላይ የተመሰረተ ሸሪዓ (ድንጋጌ) ይዞ ነው። ይህ የሆነው ለፍጡራኑ የሚበጀውንና የሚጠቅማቸውን ከሚያውቀው አላህ (ሱ.ወ.) ዘንድ የመጣ በመሆኑ ነው። አላህ (ሱ.ወ.) እንዲህ ብሏል፦

{የፈጠረ አምላክ እርሱ ዕውቀተ ረቂቁ፣ውስጠ ዐዋቂው ሲኾን፣(ምስጢርን ሁሉ) አያውቅምን?}[አል ሙልክ፡14]

እስላም ለተወሰነ ቡድን ወይም ስብስብ፣ለተለየ የቆዳ ቀለም፣ዘር ወይም ብሔር፣የመጣ ሃይማኖት ሳይሆን ለነጩና ለጥቁሩም፣ለብጫውና ለቀዩም የመጣ ነው። ጥንት ለነበረው፣ዛሬ ላለውና ወደፊት ለሚመጣውም መላው የሰው ልጅ ነው። ያሻውን ያህል የዕውቀትና የምርምር አቅም ያለው ተመራማሪ፣የእስላም ነቢይ  ይዘው በመጡት ሃይማኖት ውስጥ፣ክልላዊ ወይም ቡድናዊ ባህሪ፣የጎጠኛነት ወይም የዘረኛነት አዝማሚያ፣የአድልዖ ወይም የጭፍን ወገንተኝነት ይዘት ያለው አንዳች ነገር ማግኘት ፈጽሞ አይችልም። ይህም የእስላም አምልኮተ አላህ (ዕባዳ) ሥርዓት፣ሕግጋቱ፣ድንጋጌዎቹና የሞራል ሥርዓቱ ለመላው የሰው ዘር በሁሉም ጊዜና ስፍራ ምቹ የተደረጉ በመሆናቸው፣ጥሪያቸው የተወሰነ ቡድን ወይም ጎጥን ዒላማ ያላደረገ፣ለተለየ ሕዝብም ያልወገነ ዓለም አቀፋዊ ጥሪ ነው።

በተለይ የእስላም በመሆኑ፣ፍትሕ ወይም መልካም ስነምግባር ለአንድ ሕዝብ ወይም ለአንድ ዘመን አይበጅም ማለት የሚቻል አይደለም። በአንዳንድ ሃይማኖቶች ዘንድ ግን የክልላዊነት፣የቡድናዊነት፣ወይም የዘረኝነት አቋም በግልጽና በግላጭ ይስተዋላል። ለአብነት ያህል አይሁዶች ከሃይማኖታቸው ውጭ ካለው ሰው ጋር የሚኖራቸው በይነሰባዊ ግንኙነት ከይሁዳዊው ጋር ከሚኖራቸው የተለየና ከፍትሕ የራቀ ዘረኛ ግንኙነት ነው። አላህ (ሱ.ወ.) ይህን በማስመልከት እንዲህ ብሏል፦

{ከመጽሐፉ ሰዎችም በብዙ ገንዘብ ብታምነው ወዳንተ የሚመልስ ሰው አልለ። ከነርሱም በአንድ ድናር እንኳ ብታምነው፣ሁልጊዜ በርሱ ላይ የምትጠባበቅ ካልኾንክ በስተቀር የማይመልስ ሰው አልለ። ይኸ በመሃይምናን (በምናደርገው) በኛ ላይ ምንም መንገድ የለብንም ስለሚሉ ነው፤እነርሱ እያወቁም በአላህ ላይ ውሸትን ይናገራሉ።}[ኣሊ ዒምራን፡75]

3-የዕውቀት የግንባታና የልማት ስልጣኔ ፦

እስላም ስለ ሰው ልጅ ያለው አመለካከት ምድርን ያለማትና ያቀናት ዘንድ አላህ (ሱ.ወ.) ምትክ ወይም ኸሊፋ አድርጎ የፈጠረው መሆኑን የሚያረጋግጥ ነው። አላህ (ሱ.ወ.) እንዲህ ብሏል፦

{እርሱ ከምድር ፈጠራችሁ፤በውስጧ እንድታለሟትም አደረጋችሁ፤}[ሁድ፡61]

በተጨማሪም (ሱ.ወ.) እንዲህ ብሏል፦

{እርሱ ያ በምድር ውስጥ ምትኮች ያደረጋችሁ ነው፤የካደም ሰው ክሕደቱ በርሱ ላይ ብቻ ነው፤ከሃዲዎችንም ክሕደታቸው ከጌታቸው ዘንድ መጠላትን እንጅ ሌላ አይጨምርላቸውም፤ከሓዲዎችንም ክሕደታቸው ኪሳራን እንጂ ሌላ አይጨምርላቸውም።}[ፋጢር፡39]

በእስላም ሃይማኖት የሰው ልጆችን የሚጠቅምና ምድርን የሚያለማ ዕውቀት መማር ከተውና የተወሰነ ሰው ካልተማረው ሁሉም ሙስሊሞች ኃጢአተኛ ይሆናሉ። ሙሐመድ  ሲላኩ የሰው ልጆች በስልጣኔና በዕውቀት መስክ በከፋ ኋላ ቀርነት ውስጥ ይኖሩ የነበረ ሲሆን፣ሰዎች ምድርን ለጥቅማቸው ከመግራትና ከግንባታ ርቀው በፍልስፍና ጉዳዮችና በፍሬ ቢስ ክርክሮች ተጠምደው ነበር። ነቢዩ  የሰውን ልጅ ከዚህ ዓይነቱ አረንቋ አውጥተው የስልጣኔ፣የግንባታና የልማት ሃይማኖት በሆነው እስላም አማካይነት፣በግንባታ በመንፈስ ንጽሕና እና ምጥቀት መካከል ግጭትና ቅራኔ ሳይኖር፣አምልኮተ አላህና ልማታዊ ግንባታ በሙስሊሙ አእምሮ ውስጥ ምንም ቅራኔ ሳይፈጥሩ፣በመንፈሳዊ ሕይወቱና በሥራው መካከል የአላህን ውዴታ በማትረፍ ረገድ ምንም ግጭት ሳይኖር ብቻ ሳይሆን ይህ ሁሉ በጥምረት ለአላህ ተብሎ በርሱ መንገድ በሚሰራበት ሁኔታ ወደ ለእላይ ደረጃ ከፍ አደረጉት። አላህ (ሱ.ወ.) እንዲህ ብሏል፦

{ስግደቴ፣መገዛቴም፣ሕይወቴም፣ሞቴም፣ለዓለማት ጌታ ነው በል።}[አል አንዓም፡162]

4-የስነምግባር ስልጣኔ ፦

መልካም ስነምግባርና ጥሩ ጠባይ እስላም ውስጥ ዕባዳ ወይም አምልኮተ አላህ ነው። ነቢዩ  የተላኩበት ዓላማ መልካም ስነምግባራትን የተሟሉ ማድረግ መሆኑን ሲገልጹ እንዲህ ብለዋል፦ {የተላክሁት መልካም ስነምግባራትን ምሉእ ለማድረግ ነው።}[በማሊክ የተዘገበ] በመሆኑም የደስተኝነትና የመታደል መንገድ መልካም ስነምግባርን ሚያበረታታ የምግባረ ሰናይነትና የምስጉን ሥራዎች መንገድ ነው። መልካም ስነምግባር እስላም ውስጥ ሰው ከገዛ ራሱ ጋር፣ከአላህ ጋርና ከሌሎች ሰዎች ጋር ያለውን ግንኙነትና የመሳሰሉትን ሁሉንም የሕይወት ፈርጆች ያጠቃልል። ከሙስሊምም ሆነ ከካፍር፣ከትንሹም ሆነ ከትልቁም፣ከወንዱም ሆነ ከሴትዋ፣ከደጋፊውም ሆነ ከተቃዋሚው . . ከሁሉም ጋር የሚኖረውን ግንኙነትና አያያዝም ያካትታል። እስላም ለደግነት፣ለጀግንነት፣ለፍትሕ፣ለርህራሄ፣ለትህትና፣ለተገራ ጠባይ፣ለእውነተኛነት፣ለይሉኝታ፣ለትዕግስት፣ለቅን ልቦና፣በጎ በጎውን ለመውደድ . . ጥሪ ያደርጋል። አላህ (ሱ.ወ.) ከተቃዋሚ ጋር ቢሆን እንኳ ፍርድ ማስተካከልና ፍትሐዊ መሆን ግዴታ መሆኑን ሲያረጋግጥ እንዲህ ብሏል፦

{እላንተ ያመናችሁ ሆይ! ለአላህ ቀጥተኞች፣በትክክል መስካሪዎች ኹኑ። ሕዝቦችንም መጥላት፣ባለማስተካከል ላይ አይገፋፋችሁ፤አስተካክሉ፤እርሱ (ማስተካከል) ለአላህ ፍራቻ በጣም የቀረበ ነው። አላህንም ፍሩ። አላህ በምትሠሩት ሁሉ ውስጠ ዐዋቂ ነው።›[አል ማኢዳህ፡8]

የነቢዩ ሙሐመድን  መልእክት አስመልክቶ በርሳቸው አምኖ በተከተላቸው ላይ ብቻ ሳይወሰን ለዓለማት ሁሉ እዝነትና ጸጋ መሆናቸውን ሲያረጋግጥ አላህ (ሱ.ወ.) እንዲህ ብሏል፦

{(ሙሐመድ ሆይ!) ለዓለማትም እዝነት አድርገን እንጅ አልላክንህም።}[አል አንቢያ፡107]

ይህ ስነምግባር ከእስላማዊ ስልጣኔ ዐቢይ ክፍል ተለይቶ የማይወጣ አንድ አካሉ ብቻ ሳይሆን ዋነኛ ማእዘኑም ጭምር ነው። ምስጉን ባህርያት በሥራና በግንባታ ወይም በሌላ ማንኛውም ጥቅም ወይም በሌላ ማንኛውም ምክንያት ከአንድ ሙስሊም ፈጽሞ መራቅ አይችልም። አላህ (ሱ.ወ.) የርሱን ነቢይ የሙሐመድን  ለኛ የመልካም ስነ ምግባርና የምስጉን ባሕርያት አርአያችን ይሆኑ ዘንድ ስነምግባራቸውን ገርቷል። አላህ (ሱ.ወ.) ይህን በማስመልከት እንዲህ ብሏል፦

{ለናንተ፣አላህንና የመጨረሻውን ቀን የሚከጅል ለኾነ ሰው፣አላህንም በብዙ ለሚያወሳ፣በአላህ መልክተኛ መልካም መከተል አላችሁ።}[አል አሕዛብ፡21]

ከነቢዩ  እዝነት፣ከርህራሄያቸውና ሰዎችን ወደ መታደል መንገድ ለመምራት ካላቸው ጉጉት ከፊሉን ሲገልጽ አላህ (ሱ.ወ.) እንዲህ ብሏል፦

{ከጎሳችሁ የኾነ፣ችግራችሁ በርሱ ላይ ጥኑ የኾነ፣በናንተ (እምነት) ላይ የሚጓጓ፣በምእመናን ርኅሩህ አዛኝ የኾነ መልክተኛ በእርግጥ መጣላችሁ።}[አል ተውበህ፡128]

5- የአእምሮና የእሳቤ ስልጣኔ ፦

በእስላም ሃይማኖት ውስጥ ጥያቄ የማይቀርብበትና የማይመረመር ምንም ዓይነት ክህነታዊ ምስጢር የለም። ይልቅዬ አላህ (ሱ.ወ.) ሰዎች ስለ ተአምራቱ፣ስለ ፍጥረታቱና ስለ ሕዝቦች ሁኔታ እንዲያስተነትኑ እና እንዲመራመሩ በማዘዝ እንዲህ ብሏል፦

{(እነርሱም) እነዚያ ቆመው ተቀምጠውም፣በጎኖቻቸው ተጋድመውም፣አላህን የሚያወሱ፣በሰማያትና በምድር አፈጣጠርም የሚያስተነትኑ ፦ ጌታችን ሆይ! ይኸን በከንቱ አልፈጠርከውም፤ጥራት ይገባህ፤ከእሳትም ቅጣት ጠብቀን የሚሉ ናቸው።}[ኣሊ ዒምራን፡191]

በተጨማሪም (ሱ.ወ.) እንዲህ ብሏል፦

{እንደዚሁም ለሚያስተነትኑ ሕዝቦች አንቀጾችን እናብራራለን።}[ዩኑስ፡24]

አላህ (ሱ.ወ.) እንዲህ ብሏል፦

{በግልጽ ማስረጃዎችና በመጻሕፍት (ላክናቸው)፤ወደ አንተም፣ለሰዎች ወደነሱ የተወረደውን (ፍች) ልትገልጽላቸውና ያስተነትኑም ዘንድ ቁርኣንን አወረድን።}[አል ነሕል፡44]

በተጨማሪም አላህ (ሱ.ወ.) እንዲህ ብሏል፦

{በነፍሶቻቸው (ኹኔታ) አያስተነትኑምን? ሰማያትንና ምድርን፣በመካከላቸው ያለውንም ሁሉ፣አላህ በውነትና በተወሰነ ጊዜ እንጂ አልፈጠራቸውም፤ከሰዎቹም ብዙዎቹ በጌታቸው መገናኘት ከሓዲዎች ናቸው።}[አል ሩም፡8]

በተጨማሪም አላህ (ሱ.ወ.) እንዲህ ብሏል፦

{ይህችንም ምሳሌ ይገመግሙ ዘንድ ለሰዎች እንገልጻታለን።}[አል ሐሽር፡21]

ከዚህም በላይ አላህ (ሱ.ወ.) ዕውቀት እንዳው በግምትና በይሆናል ሳይሆን የግድ ማስረጃ ሊቀርብበት እንደሚገባ ያስተምረናል። አላህ (ሱ.ወ.) እንዲህ ብሏል፦

{እውነተኞች እንደኾናችሁ፣አስረጃችሁን አምጡ በላቸው።}[አል በቀራህ፡111]

የሃይማኖት መሪዎችና ካህናት ብቻ እንጂ ሌላው የማያውቀው ነገርም ሆነ ሊፈታ የማይችል ምንም ዓይነት ሃይማኖታዊ ምስጢርና እንቆቅልሽ እስላም ውስጥ ለም።

6-የውስጣዊና ውጫዊ ሰላም እርካታ ስልጣኔ፦

ውስጣዊ ሰላምና መረጋጋት ማለት፣በዘመናችን ስልጣኔ ውስጥ ብዙዎችን ከሚያናውጡ ውስጣዊ ግጭቶች፣የዱንያ ዓለማዊ ሕይወቱና የወዲያኛው የኣኽራ ሕይወቱ በአእምሮውና በሕሊናው ውስጥ ተጣጥመው በሚገኙበት ሁኔታ የሰው ልጅ ነጻ ሆኖ በተረጋጋ መንፈስ በሰላም መኖር ማለት ነው። አምልኮተ አላህ ከሥራና ከግንባታ ጋር የሚጣመርበት፣የመንፈስና የሥጋ ፍላጎት የሚጣጣምበት፣ሳይንስና ሃይማኖት ተደጋግፈው የሚኖሩበት ነው። በእስላማዊ ስልጣኔ ዘንድ ያለው ውስጣዊ ሰላምና መረጋጋት ከላይ የተጠቀሱትን ሁሉ በተመቻቸና ቀለል ባለ ሁኔታ በአማኙ አእምሮ ውስጥ አካቶ ከሚይዘው ተውሒድ የሚመነጭና በጉልህ የሚታይ አንዱ መገለጫው ነው። በእስላም ውስጥ ይህ ዓለማዊ ሕይወት በራሱ ግብ ወይም ዓላማ ሳይሆን ለመጭው ዘላለማዊ የኣኽራ ሕይወት የሚያገለግል ስንቅ የሚዘራበት ማሳና ወደዚያ የሚያሸጋግር መተላለፊያ ብቻ ነው። ይህም ከሚከተለው የአላህ (ሱ.ወ.) ቃል በግልጽ የምንረዳው ነው፦

{አላህም በሰጠህ ሀብት የመጨረሻይቱን አገር ፈልግ፤ከቅርቢቱም ዓለም ፋንታህን አትርሳ፤አላህም ወደ አንተ መልካምን እንዳደረገልህ (ለሰዎች) መልካምን አድርግ፤በምድርም ውስጥ ማጥፋትን አትፈልግ፤አላህ አጥፊዎችን አይወድምና፣(አሉት)።} [አል ቀሶስ፡77],

በተጨማሪም አላህ (ሱ.ወ.) እንዲህ ብሏል፦

{ሶላቲቱም በተፈጸመች ጊዜ፣በምድር ላይ ተበተኑ፤ከአላህም ችሮታ ፈልጉ፤አላህንም በብዙ አውሱ፤ልትድኑ ይከጀላልና።}[አል ጁሙዓህ፡10]

ይህም ሶላቱን ሰግደህ ካበቃህ በኋላ ሐላል ወደሆነው ዓለማዊ ሥራህ ተሰማራ፤ለአላህ ፍጹምነትን ሰንቀህና የርሱን ምንዳና ሽልማት እያሰብክ ተግተህ ሥራ ማለት ነው። ነቢዩም  ከባልደረቦቻቸው ለአንዱ እንዲህ ብለዋል፦ {የአላህን ምንዳና ውዴታውን እያሰብክ በምታወጣው ወጭ ለሚስትህ ቀለብ በምታውለው ነገር እንኳ ቢሆን ምንዳ ታገኝበታለህ።}[በማሊክ የተዘገበ] ይህም ማለት አንድ ሙስሊም ግዴታ የሆነበትን የቤቱን ወጭ ሲያወጣ እንኳ፣አላህን እያሰበ እስካደረገው ድረስ ልክ እንደ መደበኛው ዕባዳ ሁሉ ከአላህ (ሱ.ወ.) አጅር ያገኝበታል ማለት ነው። እናም በኛ ሃይማኖት ውስጥ በዱንያ ተውጠን ኣኽራን ካለመዘንጋት ግዴታ ጋር ዱንያን ከኣኽራ የሚነጥል ነገር የለም። አላህ (ሱ.ወ.) እንዲህ ብሏል፦

{እላንተ ያመናችሁ ሆይ! ገንዘቦቻችሁና ልጆቻችሁ አላህን ከማስታወስ አያታሉዋችሁ፤ይህንንም የሚሠሩ ሰዎች፣እነዚያ እነሱ ከሳሪዎቹ ናቸው።}[አል ሙናፊቁን፡9]

በተጨማሪም አላህ (ሱ.ወ.) እንዲህ ብሏል፦

{አላህም በሰጠህ ሀብት የመጨረሻይቱን አገር ፈልግ፤ከቅርቢቱም ዓለም ፋንታህን አትርሳ፤አላህም ወደ አንተ መልካምን እንዳደረገልህ (ለሰዎች) መልካምን አድርግ፤በምድርም ውስጥ ማጥፋትን አትፈልግ፤አላህ አጥፊዎችን አይወድምና፣(አሉት)።} [አል ቀሶስ፡77]

ሥራን ማፍቀር፣ሚስትን ማፍቀር፣ልጆችና ቤተሰብን ማፍቀርና መንከባከብ . . በሸሪዓው ገደብ ውስጥ፣በነቢዩ  ፈለግና አላህን በማሰብ እስከሆነ ድረስ የሃይማኖቱ አካል ተደርጎ ይቆጠራል። አላህ (ሱ.ወ.) እንዲህ ብሏል፦

{ስግደቴ፣መገዛቴም፣ሕይወቴም፣ሞቴም፣ለዓለማት ጌታ ነው በል።}[አል አንዓም፡162]

ሕይወታችን በጥቅሉ የአላህ ነው። የነፍስና የሥጋዊ ፍላጎት ጉዳይ የሆነው ክፍልም ጭምር፣ከቅርብና ከሩቅ ሰዎች ጋር፣ከደጋፊና ከተቃዋሚም ጋር፣ያለው ውጫዊ ሰላምም እንዲሁ ቅን ልቦናና መልካም ኒያ እስካለ ድረስ ለአላህ ትእዛዛት የመገዛት (የጧዓ) መገለጫ ነው። አንድ ሙስሊም ሌላ ሙስሊም ወንድሙን ሲያገኝ የሚያቀርብለት የመጀመሪያው ሰላምታም {አስላሙ ዐለይኩም ወረሕመቱሏህ ወበረካቱህ} የሚል ሲሆን {የአላህ ሰላም፣እዘነቱና በረከቶቹ ባንተ ላይ ሁን} ማለት ነው። ሁሉም ሃይማኖቶች በእስላማዊው ሥርዓት ውስጥ በደስተኛኝነትና በተደረገላቸው ጥበቃ ረክተው እንደ ኖሩት ዓይነት በየትኛውም ሌላ ሥርዓት ውስጥ ረክተው ኖረው አያውቅም። ሙስሊሞች በከፊል ወደ ኋላ በማሽቆልቆላቸው ግን ዓለማችን ብዙ ነገር አጥታለች። አላህ (ሱ.ወ.) እንዲህ ብሏል፦

{ከተከበረው መስጊድ ስለከለከሉዋችሁ ሰዎችን መጥላትም (በነሱ ላይ) ወሰን እንድታልፉ አይገፋፋችሁ፤በበጎ ነገርና አላህን በመፍራትም ተረዳዱ፤ግን በኃጢአትና ወሰንን በማለፍ አትረዳዱ። አላህንም ፍሩ፤አላህ ቅጣተ ብርቱ ነውና።}[አል ማእዳህ፡2]

7- የጥራትና የፍቅር ስልጣኔ፦

እስላማዊው ሸሪዓ ግለሰብ አባላቱ የንጹሕ ልብ፣የቅን ልቦናና የጸዳ ሕሊና ባለቤቶች እንዲሆኑ ግዴታ ይጥልባቸዋል። አላህ (ሱ.ወ.) የምእመናንን ዱዓእ አስመልክቶ እንዲህ ብሏል፦

{እነዚያም ከበኋላቸው የመጡት፣ጌታችን ሆይ! ለኛም ለነዚያም በእምነት ለቀደሙን ወንድሞቻችን ምሕረት አድርግ። በልቦቻችንም ውስጥ ለነዚያ ለአመኑት (ሰዎች) ጥላቻን አታድርግ። ጌታችን ሆይ! አንተ ርኅሩህ አዛኝ ነህና ይላሉ።}[አል ሐሽር፡10]

በተጨማሪም አላህ (ሱ.ወ.) እንዲህ ብሏል፦

{ገንዘብም ልጆችም በማይጠቅሙበት ቀን፤ወደ አላህ በንጹህ ልብ የመጣ ሰው ቢኾን እንጅ።}[አል ሹዐራ፡88-89]

ነቢዩ  እንዲህ ብለዋል፦ {እርስ በርስ አትጠላሉ፣አትመቀኛኙ፣አትዶላለቱ፣ወንድማማች የአላህ ባሮች ሁኑ እንጅ። አንድ ሙስሊም ወንድሙን ከሦስት ቀናት በላይ በማኩረፍ ሲገናኙ ይህኛው ፊቱን ማዞር፣ያኛውም ፊቱን ማዞር አይፈቀድም፤በላጫቸው አስቀድሞ ሰላምታ ሚያቀርበው ነው።}[በሙስሊም የተዘገበ] መዋደድንና ተግባቢ መሆንን ሲያበረታቱም ነቢዩ  እንዲህ ብለዋል፦ {ነፍሴ በእጁ በሆነች (አላህ) እምላለሁ፣እስክታምኑ ድረስ ጀነት አትገቡም፤እስክትዋደዱ ድረስም አታምኑም፤ይህንን የሚያጸና ነገር ልንገራችሁን? በመካከላችሁ ሰላምታን አጉልታችሁ አቅርቡ (ሰላምታን ለሁሉም አዳርሱ)።}[በእብን ማጀህ የተዘገበ] የአላህ መልክተኛ ከሰዎች በላጩ ማነው? ተብለው ሲጠየቁ ፦ {ልቡ ከክፋት የጸዳ (መኽሙሙል ቀልብ)፣አንደበቱ በጣም እውነተኛ የሆነ ሰው ሁሉ ነው።} አሉ፤{አንደበቱ በጣም እውነተኛ የሆነ} ማለት ምን እንደሆነ እናውቃለን፣{ልቡ ከክፋት የጸዳ (መኽሙሙል ቀልብ) ማለት ምን ማለት ነው? ብለው ጠየቋቸው፤እሳቸውም፦ {አላህን የሚፈራ፣ጽዱ፣ኃጢአት፣ግፍ፣ቋጠሮም ሆነ ምቀኝነት የሌለበት ልብ ነው።} ብለው መለሱ። (22)

8- መንፈሳዊ ሥጋዊ ስልጣኔ፦

እስላማዊው ስልጣኔ የመንፈስ ፍካትን ይዞ የመጣ ሲሆን፣በተመሳሳይም የሰውን ሥጋዊና ቁሳዊ ጎንም አልዘነጋም። አላህ (ሱ.ወ.) ሰውን ከሥጋና ከነፍስ ፈጥሮት በሁሉም ቁሳዊና መንፈሳዊ የሕይወት ገጽታዎች የሚያስፈልጉትን ሁሉ አስታጥቆታል። ለሥጋዊ አካሉ በምድር ላይ የሚኖርበትን ምቹ አካባቢን ሲያሰናዳለት፣ለመንፈሳዊ ጎኑ ደግሞ በመልክተኞቹ አማካይነት የተላከለትን የመለኮታዊ ወሕይ (ራእይ) ቀለብ አመቻችቶለታል። አላህ (ሱ.ወ.) የሰውን መንፈሳዊ ጎን አፈጣጠር በማስመልከት እንዲህ ብሏል፦

{ጌታህም ለመላእክት ባለ ጊዜ፣(አስታውስ) ፦ እኔ ሰውን ከሚቅጨለጨል ሸክላ፣ከሚገማ ጭቃ እፈጥራለሁ። ፍጥረቱን ባስተካከልኩትና ከመንፈሴ በነፋሁበትም (ነፍስ በዘራሁበት) ጊዜ፣ለርሱ ሰጋጆች ኾናችሁ ውደቁ።}[አል ሕጅር፡28-29]

ነፍስና ሥጋ፣መንፈስና አካል አንዱ ከሌላው በሞት ብቻ እንጂ የማይነጠል የተቃቀፉ ነገሮች ናቸው። እያንዳንዳቸውም የራሱ የሆኑ ፍላጎቶችና ጥያቄዎች አሉት። አካል በምግብ በመጠጥና በልብስ የሚኖር ሲሆን፣በአንዱ ጎን ብቻ ብንወሰን ግን ጉዳቱን በሁለቱም ጎኖች ላይ ሲንፀባረቅ እናያለን። የሰው ልጅ በመብላት ብቻ ቢወሰን የተረጋጋ መልካም ሕይወት መምራት የማይችል ደካማና ቀአቅመ ቢስ ሆኖ እናገኛዋለን፤በመጠጥና በልብስ ብቻ ቢወሰንም እንዲሁ። (23)

ከአካል ፍላጎቶች ውስጥ አንዱን ማጓደል በሁለቱም ጎኖቹ ላይ ተጽእኖ የሚያሳድር ሲሆን፣ለራሱ መኖር የሚከብደው ከመሆኑም ባሻገር ሌላኛው ጎኑን የተረጋጋ ሕይወት ይኖር ዘንድ መርዳት ይሳነዋል። መንፈስም እንዲሁ የራሱ ፍላጎቶች ሲኖሩት፣ነፍስ ያለ ፍቅር፣ያለ አበርክቶም ሆነ ያለ መስዋእትነት አትኖርም። የምታመልከው፣የምታፈቅረው፣የምትፈራው፣ተስፋ የምትጥልበትና የምትሸሽበት አምላክ ሳይኖራት እንዴትስ ትኖራለች?! የምትጠጋበትና የምትጽናናበት ሳይኖራት፣ሰላም፣አበርክቶ፣የህሊና እርካታና በሰዎች ዘንድ ፍቅርን ሳታገኝ ወና ሆና እንዴትስ ትኖራለች?! የሰው ልጅ የመንፈሱን ፍላጎቶች ካላሟላ ምግብና መጠጡንም እንደ አጓደለ በመሆኑ፣ግማሽ ጎኑ እየተራበና እየተሰቃየ መኖር እንዴት ሊጥመው ይችላል?! በጣም የሚያሳዝነው የምዕራቡ ስልጣኔ የመንፈስ ደስታንና የነፍስ እርካታን የዘነጋ በመሆኑ፣የሰው ልጅ በቁሳዊ ጎኑ የተንደላቀቀ ምችት ቢኖረውም ከደስተኝነትና ከመታደል ሕይወት ርቆ የስቃይ ኑሮ ይገፋል። የዘመናችን ስልጣኔ ሥጋና አካልን በማገልገል ረገድ የተዋጣለት ሲሆን፣ከመንፈስ የተነጠለ ነፍስ አልባ አካል ደስተኝነትን፣መድህንንም ሆነ እርካታና እርጋታን የማያውቅ መሆኑን ብቻ ሳይሆን ስልጣኔውም እውነተኛ ስልጣኔ መሆኑን ረስቷል ወይም ሆን ብሎ ዘንግቷል።

9- ለሰብአዊ ፍጡርና ለሰብአዊ መብቱ ትኩረት የሚሰጥ ስልጣኔ ፦

ሰብአዊ መብቶችን መተግበር አንድ አገር የፍትህና የእኩልነት መርሆዎችን ምን ያህል እንደሚያከብር፣የዜጎቹን መብቶችና ነጻነቶች ምን ያህል እንደሚጠብቅ ጠቋሚ መስፈርት መሆኑ በሁሉም ዘንድ ይታወቃል። ያ ሕዝብ መብቶቹን በማስከበር በኩል ያለውን ግንዛቤና የንቃተ ሕሊና ደረጃ የሚያመለክት መለኪያም ነው። የዴሞክራሲያዊ ሥርዓቶች ዋነኛው የማእዘን ድንጋይም ሰብአዊ መብቶችን ማክበር ነው።

እስላማዊው ስልጣኔ ሰብአዊ መብቶችን በማስከበር ረገድ በተጨባጭ መሬት ወርዶ በተግባር የታየ ልዩ የሆነ ተምሳሌታዊ ድል አስመዝግቧል። በዚህም ሰብአዊ መብት ባዶ መፈክር ብቻ አለመሆኑን በተግባር በማሰየት እስላማዊው ስልጣኔ ታላቅነቱን አስመስክሯል። በመሆኑም እሰላም ዘንድ ሰብአዊ መብቶችን ልዩ የሚያደርጉ አበይት ነጥቦች የሚከተሉት ናቸው ፦

1-የነዚህ መብቶች ምንጭ ሉዓላዊነትና የሕግ አውጭነት ስልጣን የአላህ (ሱ.ወ.) ብቻ መሆኑን በሚያረጋግጠው መርህ ላይ የተመሰረተ ነው። አላህ (ሱ.ወ.) እንዲህ ብሏል፦

{ፍርዱ ለአላህ ብቻ ነው፤እውነትን ይፈርዳል፤እርሱም ከፈራጆች ሁሉ በላጭ ነው በላቸው።}[አል አንዓም፡57]

እስላማዊው የሰብአዊ መብቶች ፕሮጄክት ጉዳዩን የሚመለከተው፣መለኮታዊው እይታ ይህን ሰብአዊ ፍጡርና የሚበጀውን ነገር በሚመለከትበት እይታ መሆኑ።

2- ጽናቱና በዘመን መለዋወጥም ሆነ በሁኔታዎች መቀያየር የማይለወጥ መሆኑ።

3- መብቶቹ የሚነሱት ከስምረት (እሕሳን) ደረጃ መሆኑን ትኩረት ውስጥ ማስገባት፦ እስላም ውስጥ መብቶች አንድ የአላህ አገልጋይ አላህን በመፍራትና ትእዛዛቱን በመፈጸም ረገድ የሚይዘውን የስምረት ደረጃ የሚከተሉ ናቸው። ይህ የእሕሳን ደረጃ በሚከተለው የነቢዩ  ቃል የተነገረው ነው ፦ {አላህን ልክ በዓይን እንደምታየው ሆነ እርሱን መግገዛት ነው፣አንተ ባታየውም እርሱ ያየሃልና።}[በሙስሊም የተዘገበ]

4-በሰብአዊ መብቶችና በዚህ ሃይማኖት ተፈጥሮ መካከል የተሟላ መጣጣም መኖሩ ፦ እስላም ሰብአዊ መብቶችን እንዲሁ ባዶ ቃላት አድርጎ አልተዋቸውም፤በሽሪዓዊ ሕግጋት ማእቀፍ ውስጥ በማስቀመጥ ከሸሪዓዊ ዓላማዎች አኳያ ተመልክቶ ከስነምግባራቱና ከግብረገብነት እሴቶቹ ጋር ያጣምራቸዋል። እነዚያን ስነምግባራት ማጓደልን ሰብአዊ መብቶቹን ማጓደል አድርጎ ይመለከታል። በመጨረሻም ከሃይማኖት ጋር በማስተሳሰር ምንጫቸውን መለኮታዊ ምንጭ ያደርጋል። ስለዚህም ሰብአዊ መብቶች መብቶች ብቻ ሳይሆኑ ከአንድ ሙስሊም ሃማኖታዊ ግዴታዎች አንዱ ሆነው ይቆጠራሉ። በመሆኑም እስላም ውስጥ ያለው ሰብአዊ መብቶች መዋቅር ከሃይማኖቱ መለኮታዊ ባህሪ ጋር በተጣጣመ መልኩ የተሟላ መዋቅር ነው።

5-እስላም ውስጥ ባለው የሰብአዊ መብቶች መንደርደሪያ፣የማህበረሰብ ልዕልና የግለሰቦች ልዕልና ቅርንጫፍ እንጂ በሰው ሠራሽ ሥርዓቶች ውስጥ እንደሚስተዋለው የዚህ ተቃራኒ አይደለም። አላህ (ሱ.ወ.) እንዲህ ብሏል፦

{በዚህ ምክንያት በእስራኤል ልጆች ላይ፣እነሆ ያለ ነፍስ (መግደል)፣ወይም በምድር ላይ ያለማጥፋት፣ነፍስን የገደለ ሰው፣ሰዎቹን ሁሉ እንደ ገደለ ነው፤ሕያው ያደረጋትም ሰው፣ሰዎቹን ሁሉ ሕያው እንዳደረገ ነው፣ማለትን ጻፍን፤መልክተኞቻችንም በግልጽ ተአምራት በእርግጥ መጡዋቸው፤ከዚያም፣ከዚህ በኋላ ከነሱ ብዙዎቹ በምድር ላይ ወሰንን አላፊዎች ናቸው።}[አል ማእዳህ፡32]

6-ሰብአዊ መብቶች በእስላም ውስጥ ከዘመን አኳያ ከሁሉም ቀዳሚ ነው። እስላም ለሰው ልጆች እነዚህን መብቶች ያረጋገጠው፣ዛሬ በዴሞክራሲያዊ ሥርዓቶች ውስጥ እንዳሉት የሰብአዊ መብቶች አመጣጥ መነሻና ታሪክ ዓይነት፣በፈረንሳይ በአሜሪካና በሌሎችም አገሮች እንደሆነው ከዘመናት የአመለካከት ግጭቶች፣ከመራራ ትግሎችና አብዮቶች በኋላ የተገኙ አይደሉም። የሰብአዊ መብት መርሆዎችና ድንጋጌዎች ጸንተው የመጡት ጉዳዩ ሳይነሳ፣ጥያቄ ሳይቀርብበትና ትግልም ሳይካሄድ ከአላህ (ሱ.ወ.) በተላለፈ መለኮታዊ ወሕይ ተረጋግጠው ነው።

7-በሌሎች ሥርዓቶች ውስጥ እንዳለው ዓይነት ፍልስፍናዊ ቅብ የተቀቡ ሳይሆን፣ተጨባጭና ከተግባራዊ ሕይወት ጋር የተሳሰሩ፣በሰው ልጅ እውነተኛ ፍላጎት ላይ ያነጣጠሩ ናቸው።

8-ሰብአዊ መብትን በተመለከተ እስላማዊ ሸሪዓ ልዩ የሆነባቸው ጉዳዮች ሲኖሩት ከነዚህ መካከል፦ ወላጆችና የቅርብ ዘመዶች በልጆች ላይ የሚኖራቸው መብት፣የቤተ ዘመዶች መብት፣በማሕጸን የሚገኝ ጽንስ መብት፣ሃይማኖታዊና ዓለማዊ ትምህርት የመማርና የማስተማር ግለሰባዊ መብት፣በሕጋዊ መንገድ ሀብት የማፍራትና አራጣን የመከልከል መብት፣ወደ በጎ ነገር ሁሉ ጥሪ የማድረግና የማዘዝ፣ከእኩይና ክፉ ነገሮችም የመከልከል የደዕዋ መብት ይገኛሉ።

9-የሰብአዊ መብቶች ጉዳይ እስላማዊ አቀራረብ በመሰረቱ በሰው ልጅ ክቡርነትና በአላህ (ሱ.ወ.) የማመንን ስሜት በማነሳሳት፣ከተሟላ የተቀናጀ የአነዋነዋር ሥርዓት ጋር በተጣጣመ መልኩ አላህ (ሱ.ወ.) በዚህ ዩኒቨርስ ውስጥ ያለውን ሁሉ ለሰው ልጅ የገራ በመሆኑ ጽንሰ ሐሳብ ላይ የሚሞረኮዝ ነው። የሰው ልጅ ታሪክ በየትኛውም ዘመን ሰብአዊ መብቶች ከጥቅሞች ታሳቢነት በራቀ ሁኔታ ተግባራዊ የሆኑበትን ጊዜ አይቶ አያውቅም። ባዶ መፈክሮችን ማስተጋባት ቀላል ሲሆን ከነዚህ ባዶ ጩኸቶች በስተጀርባ ያለውን ዓለማና ፍላጎት ስንመረምር ግን እውነተኛ ዓለማቸው ሰብአዊ መብት ሳይሆን የተለየ ሌላ ነገር ሆኖ እናገኛለን።

በሙሐመድ  መላክ የተሟላ ሰውኛ ስልጣኔ ለሰው ልጆች የመጣ ሆኖ ሳለ ሙስሊሞች የኋሊዮሽ የተመለሱበትና እስላማዊው ስልጣኔ በእጃቸው እያለ ዛሬ ባሉበት ሁኔታ ላይ የሆኑበት ምክንያት ምንድነው?! የሚል ጥያቄ በአንዳንዶች ይነሳ ይሆናል። ዛሬ ሙስሊሞች ያሉበት ሁኔታ የሃይማኖታቸውን እውነታ የማይወክል መሆኑን ስንረዳ ግን አግራሞቱ ይወገዳል። ብዙዎቹ ሙስሊሞች የሃይማኖታቸውን መርሆዎች፣በሕያው መጽሐፋቸውና በነቢያቸው  ሱንና ውስጥ የተካተተውን ሁሉ ወደ ጎን በመተዋቸው የኋላ ቀርነት ሰለባ ለመሆን ተጋልጠዋል። ለእስላማዊ መርሆዎቻቸው ተገዥና ታማኝ ቢሆኑ ኖሮማ ከእስላማዊው ስልጣኔ ይበልጥ ለመላው የሰው ዘር ደስተኝነትንና መታደልን ይዞ የመጣ አንድም ስልጣኔ በታሪክ ታይቶ አያውቅም። ይህን ለማረጋገጥና በሙስሊሞች ሁኔታ ማሽቆልቆል ዓለም ያጣውን ታላቅ ትሩፋት ለማወቅ፣ታሪክን ማንበብና ሙስሊም ያልሆኑ አስተዋይና ሚዘናዊ እውቅ ግለሰቦች ሳይቀሩ የሚናገሩትን ማዳመጡ ብቻ በቂ ነው።